በምእራብ ጉጂ ዞን ሱሮ ከተማ ከ1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመት የኮንትሮባንድ እቃ ተያዘ

83

ነገሌ፣ ጥር 10 ቀን 2014 (ኢዜአ) በምእራብ ጉጂ ዞን ሱሮ ከተማ ከ1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመት የኮንትሮባንድ እቃ መያዙን የዞኑ ፖሊስ መምሪያ ገለጸ፡፡

በመምሪያው የኮሙኒኬሽን ዲቪዥን ኃላፊ ዋና ሳጂን ፈዬራ ኬይረዲን  እንደገለጹት፤ ፖሊስ በህገ ወጥ መንገድ ሊዘዋወሩ ሲሉ የያዛቸው እቃዎች 2 ሺህ 783 የሞባይል ስልክ ቀፎዎች እና 265 ኪሎ ግራም የሚመዝኑ የውጭ ሀገር ጫማዎች ናቸው፡፡

እቃዎቹ  ከዞኑ ከቡሌ ሆራ ከተማ  ወደ ሱሮ በርጉዳ ከተማ የሰሌዳ ቁጥሩ ኮድ 3 - B32397 አአ በሆነ አይሱዙ የጭነት ተሽከርካሪ ሲጓጓዙ ትናንት ከረፋዱ  አምስት ሰአት  ላይ መያዛቸውን አስታውቀዋል፡፡

ፖሊስ አሽከርካሪውን በቁጥጥር ስር  አውሎ ጉዳዩን እያጣራ መሆኑን ዋና ሳጂን ፈዬራ ተናግረዋል፡፡

የዞኑ ፖሊስ ህገ ወጥ ንግድና ሌሎች ወንጀሎችን ለመከላከል የተጠናከረ  ክትትልና ቁጥጥር በማድረግ ላይ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም