ሆስፒታሉ ከፍለው መታከም ለማይችሉ የህብረተሰብ ክፍሎች የነጻ የዓይን ሞራ ቀዶ ሕክምና እየሰጠ ነው

83

አምቦ ፤ ታህሳስ 21 ቀን 2014 (ኢዜአ) የአምቦ አጠቃላይ ሆስፒታል ከፍለው መታከም ለማይችሉ 255 የማህበረሰብ ክፍሎች የነጻ የዓይን ሞራ ቀዶ ህክምና እየሰጠ ነው፡፡

ሆስፒታሉ ሕክምናውን የሚሰጠው ፍሬድ ሆል ፋውንዴሽን ከተባለ መንግሥታዊ ያልሆነ ድርጅት ጋር በመተባበር መሆኑን አስታውቀዋል።

ለአምስት ቀን እየተሰጠ ያለው ሕክምና ከፍለው መታከም የማይችሉ የዓይን ሞራ ግርዶሽ ተጠቂዎችን ከዓይነ ስውርነት ለመታደግ የሚካሄድ መሆኑን የሆስፒታሉ ሥራ አስኪያጅ አቶ ደበበ ፈጠነ ለኢዜአ ገልጸዋል።

ሕክምናው በአምቦ ከተማና አካባቢዋ ለሚገኙ የህብረተሰብ ክፍሎች እንደሚሰጥ አመልክተዋል፡፡በተጨማሪም 100 ለሚደርሱ ሰዎች የምርመራ፣ መለስተኛ ህክምናና ሌሎች አገልግሎቶች እንደሚሰጡ ተናግረዋል፡፡

ከታካሚዎች መካከል የኢሉ ገላን ወረዳ ነዋሪ አቶ ሙፍቲ አህመድ በሰጡት አስተያየት ባገኙት ነፃ የሕክምና አገልግሎት ብርሃናቸው በመመለሱ መደሰታቸውን ገልጸዋል።

ከዕድሜ መግፋት ጋር በተያያዘ በዕይታቸው ላይ ሲቸገሩ መቆየታቸውን የገለጹት ደግሞ የአምቦ ወረዳ ነዋሪ ወይዘሮ አቦነሽ ወልደሚካኤል ናቸው።

ሕክምናውን በነፃ በማግኘታቸው መደሰታቸውን ተናግረዋል።

ሆስፒታሉ ባለፉት አራት ወራት ከፍለው መታከም ለማይችሉ 386 የማህበረሰብ ክፍሎች ነጻ የአይን ቀዶ ህክምና አገልግሎት መስጠቱ ተመላክቷል።

ኢትዮጵያን እናልማ፣እንገንባ፣እንዘጋጅ

‼️

ሀገርን በዘላቂነት እናልማ

‼️

የፈረሰውን አብልጠን እንገንባ

‼️

ለማንኛውም ፈተና እንዘጋጅ

‼️
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም