የንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ለመከላከያ ሰራዊት ከ10 ሚሊዮን ብር በላይ የሚያወጣ ቁሳቁስ ድጋፍ አደረገ

63

ህዳር 19 ቀን 2014 (ኢዜአ) የንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ለመከላከያ ሰራዊት ከ10 ሚሊዮን ብር በላይ የሚያወጣ ምግብና ቁሳቁስ ድጋፍ አደረገ፡፡

ክፍለ ከተማው ድጋፉን ያደረገው ከነዋሪዎቹ በማሰባሰብ ሲሆን፤ ድጋፍን የክፍለ ከተማው ዋና ስራ አስፈጻሚ ወይዘሮ ነጻነት ዳባ ለመከላከያ ሰራዊቱ ተወካይ ኮሎኔል ሌቺሳ መገርሳ አስረክበዋል፡፡

ድጋፉም በዋናነት ለኢትዮጵያ ህልውና በግንባር ለተሰለፈው ሰራዊት የሚውል ነው፡፡

ዋና ስራ አስፈጻሚዋ በዚህን ወቅት የክፍለ ከተማው ነዋሪዎች ከዚህ ቀደም ለሰራዊቱ ድጋፍ ማድረጋቸውን አስታውሰው፤ በቀጣይም ይህን ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል፡፡

ሰራዊቱን ወክለው ድጋፉን የተቀበሉት ኮሎኔል ሌቺሳ መገርሳ በበኩላቸው"እየተደረገልን ያለው ድጋፍ ግዳጃችንን በድል ለማጠናቀቅ የሞራል መነሳሳት ፈጥሮልናል" ብለዋል፡፡

የንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ላደረገው ድጋፍም በሰራዊቱ ስም ምስጋና አቅርበዋል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም