ህዝቡ አንድ ሆኖ በመቆም ጥላቻን በፍቅር፣በቀልን በይቅርታ እየናደ አብሮነቱን ማስቀጠል አለበት

መስከረም 26/2014 (ኢዜአ) ህዝቡ አንድ ሆኖ በመቆም ከትውልድ ወደ  ትውልድ  ጥላቻን በፍቅር፣በቀልን በይቅርታ እየናደ አብሮነቱን የሚያስቀጥለው  እራሱ  መሆኑን  የኢትዮጵያ እርቀ ሰላም ኮሚሽን ገለጸ፡፡

የኢትዮጵያ እርቀ ሰላም ኮሚሽን ለጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ  አህመድ  የእንኳን ደስ  አለዎት  መልእክት  አስተላልፏል።

የኢትዮጵያ እርቀ ሰላም ኮሚሽን ለጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድ  እና   ህዝብ ለማገልገል  ለተመረጡ  የስራ ሃላፊዎች የእንኳን ደስ  አለዎት  መልእክት  አስተላልፈዋል፡፡

የኢትዮጵያን አሸናፊ አድርጎ በህዝብ ይሁንታን ያገኘ  መንግስት መስከረም 24/2014 መመስረቱ አስታውሶ ፤ይህን ህዝብ ለመምራትና ለማገልገል መመረጥ እድል ነው ብሏል፡፡

ህዝቡ አንድ ሆኖ በመቆም ከትውልድ ወደ ትውልድ ጥላቻን በፍቅር፣በቀልን በይቅርታ እየናደ አብሮነቱን የሚያስቀጥለው ህዝብ መሆኑን  በመግለጫው አንስቷል፡፡

በህዝብ የተመረጡ የመንግስት የስራ ሃላፊዎች ኢትዮጵያ ያለችበትን ሁኔታ ባገናዘበ መልኩ የህዝብ አገልጋይነታቸው በብቃት እንደሚወጡ  ያለውን እምነት ገልጿል።

ድንቅ እሴት፣ቋንቋ፣ባህልና ማንነት ያለው ህዝብ በጠንካራ መሰረት ላይ የተገነባ ኢትዮጵያዊነት ወደ ተሻለ ከፍታ እንደሚወስድ  በመተማመን ዲሞክራሲያዊ  ምርጫና የመንግስት ምስረታ መደረጉ አስደሳች ነው ብሏል፡፡

ኮሚሽኑ የእርቀ-ሰላም ስራዎቹን ለመጀመር የአገር መረጋጋት አስፈላጊነት የታመነ በመሆኑ የተቋቋመበትን አላማ ከግብ ለማድረስ የሁላችንም ትብብር የሚጠይቅ በመሆኑ ድጋፋችሁ አይለየን ብሏል በመግለጫው።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም