ሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ከ6 ሺህ 700 በላይ ተማሪዎችን በመጪው ቅዳሜ ያስመርቃል - ኢዜአ አማርኛ
ሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ከ6 ሺህ 700 በላይ ተማሪዎችን በመጪው ቅዳሜ ያስመርቃል

ሀዋሳ መስከረም 6/2014 (ኢዜአ) ሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ለ22ኛ ጊዜ በተለያየ የሙያ መስክ በመጀመሪያ ፣ ሁለተኛና ሶስተኛ ዲግሪ መርሀ ግብር 6 ሺህ 793 ተማሪዎች በመጪው ቅዳሜ ያስመርቃል።
የዩኒቨርሲቲው የውጭ ግንኙነትና ኮሙኒኬሽን ጽህፈት ቤት ዳይሬክተር ጄኔራል ረዳት ፕሮፌሰር ማቲዮስ ወልደጊዮርጊስ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ለምረቃ የሚበቁት አምና በኮሮና ቫይረስ ክስተት ምክንያት ተቋርጦ የነበረውን ትምህርት ቀጥለው በአግባቡ በማጠናቀቃቸው ነው።
ከተመራቂዎቹ 799 በሁለተኛ ዲግሪ፣ 14 በሶስተኛ ዲግሪና 12 ስፔሻሊቲ መርሀ ግብር፤ ቀሪዎቹ በመጀመሪያ ዲግሪ ትምህርታቸውን ያጠናቀቁ ናቸው።
ዩኒቨርሲቲው ባሉት ሰባት ኮሌጆችና ሁለት ኢንስቲትዩቶች በመደበኛና ተከታታይ የትምህርት መርሃ ግብሮች ከ41 ሺህ ተማሪዎችን በማስተማር ላይ እንደሚገኝም ተመልክቷል።