በጎንደር ከተማ ህገ-ወጥ የነዋሪነት መታወቂያ ሲያዘጋጁ የነበሩ አራት ተጠርጣሪዎች ተያዙ - ኢዜአ አማርኛ
በጎንደር ከተማ ህገ-ወጥ የነዋሪነት መታወቂያ ሲያዘጋጁ የነበሩ አራት ተጠርጣሪዎች ተያዙ
ጎንደር፣ ነሐሴ 26 ቀን 2013 (ኢዜአ) በጎንደር ከተማ በአንድ የግል ማተሚያ ድርጅት ውስጥ በህገ-ወጥ መንገድ የተዘጋጁ 544 መታወቂያዎችን ከአራት ተጠርጣሪ ግለሰቦች ጋር በቁጥጥር ስር ማዋሉን የከተማው የሰላምና ደህንነት መምሪያ አስታወቀ፡፡
የመምሪያው የመረጃና ክትትል ባለሙያ አቶ ስንታየሁ ተገኘ ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ ህገ-ወጥ መታወቂያዎቹ የተያዙት በማተሚያ ድርጅቱ ውስጥ በተደረገ ድንገተኛ ቁጥጥር ነው፡፡
መታወቂያዎቹ በሀሰተኛ ደብዳቤና ምንም አይነት የይታተምልን የትእዛዝ ደብዳቤ በሌለበት ሁኔታ ታትመው እጅ ከፍንጅ የተያዙ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡
ህገ-ወጥ መታወቂያዎቹ በላይ አርማጭሆ ወረዳ የአምበዞ ቀበሌ 200 እንዲሁም በምእራብ ጎንደር ዞን መተማ ወረዳ ጉባይ ጀጀቢት ቀበሌ ስም 198 የተዘጋጁ መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡
በተጨማሪም በማእከላዊ ጎንደር ዞን መሃል አርማጭሆ ወረዳ ፈልፈል ቀበሌ ስም የተዘጋጁ 146 ህገ-ወጥ መታወቂያዎች በማተሚያ ቤቱ ታትተመው ለስርጭት በዝግጅት ላይ እንዳሉ መያዙን ገልፀዋል።
ከህገ-ወጥ የመታወቂያ ህትመቱ ጋር በተያያዘም የማተሚያ ቤቱን ባለቤት ጨምሮ አራት ተጠርጣሪ ግለሰቦች በህግ-ቁጥጥር ስር ውለው በፖሊስ ምርመራ መጀመሩን ገልጸዋል፡፡
"ካለንበት ወቅታዊ የህልውና ዘመቻ ጋር በተያያዘ ህገ-ወጥ መታወቂያዎቹ አሸባሪው ህወሃት በከተሞች ሰርጎ ገብቶ የሽብር ተግባር ለመፈጽም እንዲችል ምቹ ሁኔታ የሚፈጥሩ ናቸው" ሲሉም ተናግረዋል፡፡
ህዝቡ ከፀጥታ አካላት ጋር የጀመረውን ቅንጅታዊ አሰራር አጠናክሮ የሽብር ቡድኑ የጥፋት ተልእኮ መሳሪያ በመሆን የከተማውን ሰላምና ደህንነት ለማደፍረስ የሚሰሩ ግለሰቦችን አጋልጦ እንዲሰጥ ጥሪ አቅርበዋል።