በኢትዮጵያ ለሚገኙ የዲፕሎማቲክ ማኅበረሰብ አባላት የአረንጓዴ አሻራ ትግበራን የተመለከተ ገለጻ ተደረገ - ኢዜአ አማርኛ
በኢትዮጵያ ለሚገኙ የዲፕሎማቲክ ማኅበረሰብ አባላት የአረንጓዴ አሻራ ትግበራን የተመለከተ ገለጻ ተደረገ

አዲስ አበባ፤ ግንቦት 13/2013(ኢዜአ) የውሃ፣ መስኖና ኢነርጂ ሚኒስትር ዶክተር ኢንጂነር ስለሺ በቀለ የ2013 የአረንጓዴ አሻራ ትግበራን አስመልክተው በኢትዮጵያ ለሚገኙ የዲፕሎማቲክ ማኅበረሰብ አባላት ገለጻ አደረጉ።
ሚኒስትሩ በገለጻቸው የአረጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ፋይዳና አተገባበርን በሚመለከት ማብራሪያ ሰጥተዋል።
ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር አማካኝነት ለአፍሪካ ብሎም ለዓለም አካባቢ ጥበቃ ያላትን ቁርጠኛ አቋምም ገልጸዋል።
የገለጻው ዓላማ የዲፕሎማቲክ ማኅበረሰቡ የመርሃ-ግብሩን ሁለንተናዊ ፋይዳና ሂደት ተገንዝቦ ከኢትዮጵያ ጎን በመሰለፍ የበኩሉን ድርሻ እንዲወጣ ማድረግ መሆኑም ተጠቁሟል።
ከሁለት ዓመታት በፊት የተጀመረው የኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ዘንድሮም "ኢትዮጵያን እናልብሳት" በሚል መርህ ይተገበራል።
በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር 7 ቢሊዮን ችግኞችን ለመትከል ነው የታቀደው።
ከዚህ ውስጥ 1 ቢሊዮን ችግኞች ለጎረቤት አገራት የሚቀርቡ ሲሆን ይህም ኢትዮጵያ ከአፍሪካ ጎን ለጎን በጋራ የመልማት እቅድን ለማገዝ የድርሻዋን ለመወጣት ያለመ ነው።
በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር በአጠቃላይ ከ25 ሚሊዮን በላይ ዜጎች ይሳተፋሉ ተብሎ ይጠበቃል።