ቀጥታ፡

የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ባለፉት ዘጠኝ ወራት 13 ነጥብ 4 ቢሊዮን ብር ትርፍ አገኘ

ሚያዚያ 20/2013 (ኢዜአ) የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ባለፉት ዘጠኝ ወራት 13 ነጥብ 4 ቢሊዮን ብር ትርፍ ማግኘቱን የባንኩ ፕሬዝዳንት አቤ ሳኖ ገለፁ። የባንኩ አጠቃላይ ተቀማጭ የገንዘብ መጠንም 698 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር ደርሷል።

የባንኩ የዘጠኝ ወራት እቅድ ክንውንና አፈጻጸም በዛሬው እለት የተገመገመ ሲሆን ባንኩ ካገኘው 55 ነጥብ 8 ቢሊዮን ብር ገቢ 13 ነጥብ 4 ቢሊዮኑ የተጣራ ትርፍ መሆኑ ተገልጿል።

የባንኩ ፕሬዝዳንት አቶ አቤ ሳኖ እንደገለጹት ባንኩ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከ102 ቢሊየን ብር በላይ ተቀማጭ ገንዘብ ያገኘ ሲሆን አጠቃላይ የባንኩ የተቀማጭ የገንዘብ መጠንም 698 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር ደርሷል።

ባንኩ በዘጠኝ ወራት የተቀማጭ ገንዘብ መጠኑን በ124 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር ለማሳደግ አቅዶ በ102 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር በማሳደግ የእቅዱን 82 ነጥብ 4 በመቶ አሳክቷል ብለዋል።

በዚህም የባንኩ በአጠቃላይ የተቀማጭ የገንዘብ ክምችት የበጀት አመቱ ሲጀመር ከነበረው ብር 595 ነጥብ 5 ቢሊዮን ወደ 698 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር ማደጉን ፕሬዚዳንቱ ተናግረዋል፡፡ 

ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከወጪ ንግድ 216 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር፤ ከውጭ ሐዋላ ደግሞ 2 ነጥብ 13 ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር ገቢ መገኘቱም ተገልጿል፡፡

ባንኩ ከሰጣቸዉ የተለያዩ ብድሮች 36 ነጥብ 9 ቢሊዮን ብር በመሰብሰብ የእቅዱን 54 ነጥብ 5 በመቶ አሳክቷል ብለዋል፡፡ 

የአገልግሎት ተደራሽነትን በማስፋት ረገድ በበጀት አመቱ ዘጠኝ ወራት 62 አዳዲስ ቅርንጫፎችን መክፈቱንም ይፋ አድርገዋል።

በዚህም አጠቃላይ የባንኩን የቅርንጫፎች ቁጥር 1 ሺህ 666 ደርሷል።

አዲስ በተከፈቱት ቅርንጫፎች 885 ነጥብ 9 ሚሊዮን ብር ተጨማሪ ተቀማጭ ገንዘብ መሰብሰብ መቻሉንም ገልጸዋል።

በበጀት አመቱ 4 ነጥብ 27 ሚሊዮን አዳዲስ ሂሳቦች ተከፍተዉ አጠቃላይ የተቀማጭ ደንበኞች ሂሳብ ቁጥር 29 ነጥብ 37 ሚሊዮን ደርሷል፡፡

የባንኩን አሰራር ለማዘመን የተለያዩ ፕሮጀክቶች በመቅረጽ በመተግበር ላይ እንደሆነም ፕሬዝዳንቱ ገልጸዋል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም