በአዲስ አበባ ከተማ ለ500 ሺህ ተማሪዎች የልደት ሰርተፍኬት ሊሰጥ ነው

162

አዲስ አበባ፣ ጥር 1 /2013 ( ኢዜአ) የአዲስ አበባ ወሳኝ ኩነቶች ምዝገባ መረጃ ኤጀንሲ በመዲናዋ ለ500 ሺህ ተማሪዎች የልደት ሰርተፍኬት ለመስጠት መዘጋጀቱን አስታወቀ። 

በኢትዮጵያ ከ1952 ዓ.ም ጀምሮ የወሳኝ ኩነቶች ምዝገባ የፍትሀ ብሄር አካል አድርጎ ያስቀመጠው ቢሆንም፤ ህጉ ከ50 ዓመታት በላይ ተፈጻሚ ሳይሆን ቆይቷል።

የአዲስ አበባ ወሳኝ ኩነት ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ታከለ ነጫ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ እንዳሉት፤ ለተማሪዎቹ ሰርተፊኬቱን ለመስጠት ዝግጅቱ ተጠናቋል።

በዚህም ኤጀንሲው ሰርተፍኬቱን ለመስጠት ከከተማ አስተዳደሩ ትምህርት ቢሮ ጋር ስምምነት ላይ መደረሱን ገልጸዋል።

የትምህርት ቤቶች ርዕሳነ መምህራንም ግንዛቤ እንዲጨብጡ ተደርጓል ብለዋል ።

የልደት ሰርተፍኬቱን ለመስጠት ምዝገባ በኮልፌ፣ በአዲስ ከተማ እና ጉለሌ ክፍለ ከተሞች መጀመሩን የገለጹት ዶክተር ታከለ በሌሎች  ክፍለ ከተሞችም ይቀጥላል ብለዋል።

ምዝገባው የዘመናዊነት መገለጫ መሆኑን ያስረዱት ዶክተር ታከለ፣ በመስኩ የሚታየውን የግንዛቤ ጉድለት ለማስተካከል እየተሰራ መሆኑንም ገልጸዋል።

ምዝገባው በቀጣይ በሴቶች ማህበራት፤በፖሊስና በመንግሥት መሥሪያ ቤቶች በዘመቻ መልክ እንደሚከናወንም ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም