ሕገ-ወጥ የገንዘብ ዝውውር ከአገራዊ ኪሳራ ባሻገር ዓለምአቀፋዊ ተፅዕኖ ያስከትላል

67

አዲስ አበባ፣ ታህሳስ 26 ቀን 2013 (ኢዜአ) ሕገ-ወጥ የገንዘብ ዝውውርን በተቀናጀ አሰራር መከላከል ካልተቻለ አገራዊ ኪሳራ ብቻ ሳይሆን ዓለምአቀፋዊ ተፅዕኖም እንደሚያስከትል የፋይናንስ ደህንነት መረጃ ማዕከል አስታወቀ።

ማዕከሉ ከአገራዊ ለውጡ በፊት በአዋጅ የተሰጠውን ሃላፊነት እንዳይወጣ ጫና ይደረግበት እንደነበረም ተገልጿል።

የፋይናንስ ደህንነት መረጃ ማዕከል ባለሙያዎች ሕገ-ወጥ የገንዘብ ዝውውርን መከላከል ለተወሰኑ ተቋማት የሚተው ሳይሆን ድርጊቱን ማጋለጥ የሁሉም ዜጋ ሃላፊነት እንደሆነ ይናገራሉ።

የማዕከሉ የክትትልና ቁጥጥር ቡድን መሪ አቶ ሙሉጌታ ተመስገን "ድርጊቱ በአገር ላይ የሚያስከትለው ኪሳራ እንዳለ ሆኖ ኢንቨስትመንትን ጨምሮ ብድርና እርዳታን በማሳጣት ዓለምአቀፋዊ ተፅእኖ ያስከትላል" ይላሉ።

ዓለም አቀፉ የፋይናንስ ተቆጣጣሪ ግብረ ሃይል በአገሮች የፋይናንስ ደህንነት ላይ የሚያወጧቸውን ሕጎችና መመሪያዎች በየጊዜው በመገምገም ያሉበትን ሁኔታ ይፋ ያደርጋል።

ይህ ግብረ ሃይል በኢትዮጵያ የፋይናንስ ደህንነት ሕግና አተገባበር ላይ ባደረገው ግምገማ አስጊ ሁኔታ ውስጥ እንዳለች አስታውቆ እንደነበረም አስታውሰው፤ በአሁኑ ወቅት ከአስጊ ሁኔታ መውጣት መቻሏን ገልጸዋል።

ነገር ግን ሕገ-ወጥ የገንዘብ ዝውውርን በቅንጅት መቆጣጠርና መከላከል ካልተቻለ ተመልሳ ወደ ስጋት ልትገባ እንደምትችል አስጠንቅቀዋል።

የፋይናንስ ወንጀሎች ትንተና ቡድን መሪ አቶ ገበየሁ ጉደታ በበኩላቸው ማዕከሉ በዓለም አቀፍ ተቋማት የሚካሄደውን ግምገማ ለማሟላት እንጂ ትክክለኛ ተልዕኮውን እንዲወጣ ተደርጎ እንዳልተደራጀ ተናግረዋል።

ተቋሙ ለአገር ከፍተኛ ጠቀሜታ ያለው ቢሆንም ተልዕኮውን በአግባቡ እንዳይወጣ ከለውጡ በፊት በነበሩ አመራሮች ጣልቃገብነትና ጫና ይደርስበት እንደነበረ አስታውሰዋል።

ተቋሙ የተጣለበትን ሃላፊነት በአግባቡ እንዳይወጣ መደረጉ በሌሎች ዘንድ እምነት እንዳሳጣውም ገልጸዋል።

በአሁኑ ወቅት ከሕገወጥ የገንዘብ ዝውውር ጋር ተያይዞ የሚፈጸም የወንጀል ድርጊትን ለመቀነስ ከተለያዩ ተቋማት ጋር እየተሰራ ስለመሆኑ ባለሙያዎቹ ገልፀዋል።

ከኢትዮጵያ ከፍተኛ መጠን ያለው ገንዘብ በሕገወጥ መንገድ ወደተለያዩ አገሮች እንደሚሸሽ መረጃዎች ያመላክታሉ።


የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም