የህዳሴ ግድብ የሶስትዮሽ ድርድር በሱዳን ጥያቄ መሰረት በድጋሜ መራዘሙ ተገለጸ

77

 አዲስ አበባ  ነሀሴ 4/2012 (ኢዜአ) በዛሬው ዕለት እንዲካሄድ ታቅዶ የነበረው የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የሶስትዮሽ ድርድር በሱዳን ጥያቄ መሰረት በድጋሜ ለአንድ ሳምንት መራዘሙን የውሃ፣ መስኖና ኢነርጂ ሚኒስቴር አስታወቀ።

ሚኒስቴሩ ለኢዜአ በላከው መግለጫ እንደገለጸው፤ የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብን በተመለከተ በዛሬው ዕለት እንዲካሄድ ታቅዶ የነበረው የኢትዮጵያ፣ ሱዳን እና ግብጽ የድርድር ስብሰባ በሱዳን ጥያቄ መሰረት ለአንድ ሳምንት ተራዝሟል።

ሃገራቱ ድርድሩን በመቀጠል የአፍሪካ ህብረት ጉባኤ ቢሮ ስብሰባ በተካሄደ ሁለት ሳምንታት ጊዜ ውስጥ የመካከለኛ እና የመጨረሻ ሪፖርት ለህብረቱ ሊቀመንበር ሪፖርት እንዲያቀርቡ ይጠበቅ ነበር፡፡

ሆኖም ግብጽ እና ሱዳን ባቀረቡት ማራዘሚያ ምክንያት ባለፉት ሁለት ሳምንታት ድርድር ሳይካሄድ ቀርቷል፡፡

የአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ጉባዔ ጽ/ቤት እ.ኤ.አ. በጁላይ 24 ቀን 2020 ባወጣው መግለጫ እንዲሁም የሶስቱ ሀገራት የውሃ ጉዳይ ሚኒስትሮች በሐምሌ 27 ቀን 2012 ዓ.ም. ባደረጉት ስብሰባ በጋራ ሰነድ ላይ ለመስራት በደረሱት መግባባት መሰረት ኢትዮጵያ የበኩሏን የግድብ ሙሌት ደምብ ማቅረቧ ይታወሳል፡፡

ድርድሩ በመጪው ሰኞ ነሐሴ 11 ቀን 2012 እንደሚቀጥል ያመለከተው መግለጫው፤ በድርድር የሚደረስበት ስምምነት ብቸኛ አማራጭ በመሆኑ ኢትዮጵያ ለድርድሩ ውጤታማነት አበክራ ትሰራለች ብሏል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም