"የትግራይ ክልል ምክር ቤት ምርጫ ይካሄድ ብሎ መወሰኑ ህገ መንግስቱን የሚጻረር ስለሆነ መንግስት የምርጫ ቦርድን ውሳኔ አክብሮ ያስፈጽማል".... አቶ ንጉሱ ጥላሁን

150

አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2012 (ኢዜአ) "የትግራይ ክልል ምክር ቤት ምርጫ ይካሄድ ብሎ መወሰኑ ህገ መንግስቱን የሚጻረር ስለሆነ መንግስት የምርጫ ቦርድን ውሳኔ አክብሮ ያስፈጽማል" ሲሉ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት ፕሬስ ሴክሬታሪያት ሃላፊ አቶ ንጉሱ ጥላሁን አስታወቁ።

ምርጫን የማስፈፀም ስልጣን የተሰጠው በህግመንግስቱ አንቀፅ 102 የተቋቋመው ምርጫ ቦርድ ስለሆነ ሌላ አካል በዚህ ጉዳይ ላይ ጣልቃ ልግባ ቢል ከስልጣን ገደቡ በላይ የምርጫ ቦርድን ስልጣን መጋፋት እና መዳፈር ስለሚሆን መንግስት የምርጫ ቦርድን ውሳኔ አክብሮ ይፈጽማል ነው ያሉት።

መከላከያ ሰራዊቱ ነጻና ገለልተኛ ሆኖ "የሃገርን ሉዋላዊነትና ህገመንግስቱን እንደሚያስከብር ሁሉ ምርጫ ቦርድም የተሰጠውን ህገመንግስታዊ ስልጣን ሁሉም አካል ሊያከብር ይገባል" ሲሉም ተናግረዋል።

ሀላፊው አቶ ንጉሡ ጥላሁን ለኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት እንደተናገሩት፤ በህገመንግስቱ መሰረት ምርጫን የማስፈጸም ስልጣን ለአስፈጻሚው ስላልተሰጠ ከምርጫ ጋር በተያያዘ ማንኛውንም ነገር ሊያደርግ የሚችለውና ህገመንግስታዊ ስልጣን ያለው ምርጫ ቦርድ ብቻ ነው፡፡

“አስፈፃሚ አካሉ በምርጫ ቦርድ ስራ እና ውሳኔ ጣልቃ በመግባት ቢፈትፍት ያለ ሀላፊነቱ መንቀሳቀስ ስለሆነ መንግስት የምርጫ ቦርድን ውሳኔ ያከብራል፣ይፈፅማል” ነው ያሉት አቶ ንጉሡ፡፡

በኢትዮጵያ ታሪክ ምርጫ ቦርድ የተሸለ እና ገለልተኛ ሆኖ እንዲቋቋምና ለእውነተኛ ዴሞክራሲ መጎልበት በር አድንዲከፍት ሆኖ ተደራጅቷል ያለት አቶ ንጉሡ፤ የክልልም ሆነ የፌዴራል መንግስት በዚህ ጉዳይ ላይ ጣልቃ ልግባ ቢል ከስልጣን ገደቡ በላይ የምርጫ ቦርድን ስልጣን መጋፋት እና መዳፈር ይሆናል ሲሉ ነው ያብራሩት።

እንደ አቶ ንጉሡ ገለጻ፤ የኢትዮጵያ መንግስት በአሁኑ ወቅት ዋነኛ ትኩረቱ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ በመከላከል የህዝብን ደህንነት መጠበቅ፣ የህዳሴ ግድብን በተመለከተ የሚገጥመን የማደነቃቀፍ ፈተና በማለፍ ውሀ መሙላት መጀመር እና ለጥቅም ማብቃት እንዲሁም ወረርሽኙ ሊያደርስ የሚችለውን ኢኮኖሚያዊ ጉዳት ሊቀንሱ የሚችሉ ስልቶችን ነድፎ መረባረብ ነው፡፡

የምርጫው ጉዳይ ገለልተኛው እና በህገመንግስቱ ስልጣን የተሰጠው ምርጫ ቦርድ ስራ ይሆናል ያሉት አቶ ንጉሡ፤ ምርጫ ቦርድ ደግሞ በህገ መንግስቱ በተሰጠው ስልጣን መሰረት የሚያደርገውን ያደርጋል የሚል እምነት አለኝ ሲሉ አስታውቃዋል።

ይህም ልክ መከላከያ ሰራዊቱ ገለልተኛ ሆኖ የሀገርን ሉዋላዊነት እና ህገመንግስቱን እንደሚያስከብር ሁሉ ምርጫ ቦርድም በህገመንግስቱ የተሰጠውን ስልጣንና ሃላፊነት ያስከብራል ማለት እንደሆነ አብራርተዋል።

የትግራይ ክልል ምክር ቤት በትናንትናው ዕለት የክልሉን ምክር ቤት ምርጫ በዘንድሮው አመት አካሂዳለሁ ብሎ መወሰኑ ይታወሳል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም