ዶክተር ሁሴን ሃሺ ቃሲም የሱማሌ ክልል የፍትህና ጸጥታ ቢሮ ሀላፊ ሆነው ተሾሙ

137

መጋቢት 25 /2012 (ኢዜአ) ዶክተር ሁሴን ሃሺ ቃሲም የሱማሌ ክልል የፍትህና ጸጥታ ቢሮ ሀላፊ ሆነው መሾማቸው ተገለጸ፡፡

ሹመቱ በክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳደር ሙስጣፌ ኡመር የተሰጠ ነው።

ዶክተር ሁሴን በዓለም ዓቀፍ የልማት ተቋም የሰላም ግንባታና ፖሊሲ ትንተናዎች ዘርፍ ላለፉት 19 ዓመት ያገለገሉ መሆናቸው የግል ማህደራቸው ያስረዳል።

ዶክተር ሁሴን ሃሺ ከ2008 ዓ.ም ጀምሮ የክልሉ ፕሬዝደንት ከፍተኛ አማካሪ ሆነው ሲያገለግሉ መቆየታቸው ተነግሯል።

በሌላ በኩል ዶክተር ሁሴን  በአሜሪካና ካናዳ በህዝብ አስተዳደር እንዲሁም በምስራቅ አፍሪካ በዓለም አቀፍ የልማት  ኤጄንሲ ተቋም ውስጥ በአገረ ግንባታ፣ በአስተዳደርና በሰላም ግንባታና ማረጋጋት ዘርፍ ሲያገለግሉ እንደነበር ተጠቅሷል።

ዶክተር ሁሴን ቃሲም በስነ ህዝብ ፖሊሲ የዶክትሬት ዲግሪ ያላቸው ሲሆን ከሲቪል ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ሚኒሶታ፣ ከያለ ዩኒቨርሲቲ እና ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ኦታዋ የተለያዩ ሙያዊ ስልጠናዎችን የወሰዱ መሆናቸው ተገልጿል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም