ምክር ቤቱ የተለያዩ ሹመቶችን አፀደቀ

91
ባህርዳር፤ የካቲት 10/2012(ኢዜአ) የአማራ ክልል ምክር ቤት አስቸኳይ ጉባኤ የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንትን ጨምሮ የተለያዩ የስራ ኃላፊዎችን ሹመት አፀደቀ። የምክር ቤቱ አምስተኛ ዙር አምስተኛ ዓመት  የስራ ዘመን አንደኛ አስቸኳይ ጉባኤ ያጸደቃቸው የስራ ኃላፊዎች  ሹመት በክልሉ ርዕሰ መስተዳደር አቅራቢነት ነው። ተሿሚዎቹም፡- 1/ አቶ አብየ ከሳው - የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት ፣ 2/ አቶ ሃይለሰየሱስ ተስፋ ማሪያም -  የጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ምክትል ፕሬዚዳንት፣ 3/ ዶክተር የሽመቤት ደምሴ - የክልሉ ዋና ኦዲተር መስሪያ ቤት ዋና ኦዲተር 4/ ዶክተር ሙሉዩነሽ አበበ - በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማዕረግ  የማህበራዊ ክላስተር አስተባባሪና የክልሉ ሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ኃላፊ፣ 5/ አቶ ሲሳይ ዳምጤ- የክልሉ ሰላምና ደህንነት ጉዳዮች ቢሮ ኃላፊ፣ 6/ አቶ ተፈራ ወንድማገኝ -  የክልሉ ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት ቢሮ ኃላፊ እና 7/ዶክተር ሰይድ ኑሩ - በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማዕረግ  የኢኮኖሚ ክላስተር አስተባባሪና የከተማ ልማትና        ቤቶች  ኮንስትራክሽን ቢሮ ኃላፊ ናቸው። ተሿሚዎቹ በምክር ቤቱ ጉባኤ ፊት ቀርበው በህዝብ የተሰጣቸውን ኃላፊነት በታማኝነትና በህግ መሰረት ለመወጣት ቃለ መሀላ ፈፅመዋል። ርዕሰ መስተዳደር አቶ ተመስገን ጥሩነህ  በእጩነት አቅርበው የተሾሙት የስራ ኃለፊዎቹ ክልሉን በተሻለ እውቀትና ልምድ ያግዛሉ ተብለው የታመነባቸው  መሆኑን ገልጸዋል። ምክር ቤቱ ቀደም ሲልም  ዶክተር ፈንታ ማንደፍሮን የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳደር አድርጎ መሾሙ ይታወቃል። ጉባኤው  ከሰዓት በኋላ  በቀጣይ ስራ አቅጣጫዎች ዙሪያ እንደሚመክር ይጠበቃል።      
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም