የትራፊክ ቅጣት ክፍያ በሁሉም የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ቅርንጫፎች ተጀመረ

96
ኢዜአ ታህሳስ 8/2012 የትራፊክ ህግ ጥሰት የሚፈፅሙ አሽከርካሪዎች ላይ የሚጣለው የቅጣት ክፍያ በሁሉም የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ቅርንጫፎች መፈጸም የሚቻልበት አሰራር መጀመሩን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትራፊክ ማኔጅመንት ኤጀንሲ አስታወቀ። ኤጀንሲው ለኢዜአ በላከው መግለጫ እንዳስታወቀው በኤጀንሲው የሚሰጡ አገልግሎቶችን በቴክኖሎጂ የተደገፉና ተደራሽ ለማድረግ እየተሰራ ይገኛል። በተለይም ከትራፊክ ቅጣት አሰባሰብ ጋር ተያይዞ የነበረውን ችግር ለመፍታትና የቅጣት መረጃ አያያዝን ስርዓት ለማዘመን ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጋር ስምምነት ተደርጎ ዝግጅት ሲደረግ መቆየቱ ተገልጿል። በአሁኑ ወቅትም የዝግጅት ስራው ተጠናቆ ከዛሬ ጀምሮ በአዲስ አበባ በሚገኙ ሁሉም የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ቅርንጫፎች የቅጣት ክፍያ መፈፀም ተጀምሯል። ይህ አሰራር በንግድ ባንክ ብቻ ሳይወሰን ደንበኞች የትራፊክ ቅጣት ክፍያቸውን በሌሎች የግል ባንኮችና በኢትዮ-ቴሌኮም አገልግሎት አማራጮች ተጠቅመው እንዲከፍሉ እየተሰራ መሆኑም ተመልክቷል። ኤጀንሲው ከአዲሱ አሰራር በተጨማሪ የቅጣት ክፍያዎችን ተንቀሳቃሽ ስልክ በመጠቀም በ'ሲ ቢ ኢ' ብር የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የክፍያ መተግበሪያ አማካኝነትም መክፈል የሚችሉበት አሰራር ለመዘርጋትም እየተሰራ እንደሚገኝም ኤጀንሲው አስታውቋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም