ተቋሙ በአገልግሎት አሰጣጥ የሚስተዋሉ ችግሮችን መፍትሄ ሊሰጣቸዉ ይገባል - ባለድርሻ አካላት

67
ኢዜአ ህዳር 29 / 2012 ዓ.ም ተቋሙ በአገልግሎት አሰጣጥ የሚስተዋሉ ችግሮችን መፍትሄ ሊሰጣቸዉ እንደሚገባ ባለድርሻ አካላት ጠቁመዋል፡፡ ተቋሙ በአገልግሎት አሰጣጥ የሚስተዋሉ ችግሮችን መፍትሄ ሊሰጣቸው እንደሚገባ ባለድርሻ አካላት ጠቆሙ፡፡ በደቡብ ክልል ኤሌክትሪክ አገልግሎት የሆሳዕና ዲስትሪክት ከባለድርሻ አካላት ጋር የምክክር መድረክ በሆሳዕና ከተማ ዛሬ አካሂዷል፡፡ በመድረኩ የተገኙት የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አማካሪ አቶ ታደለ ግርማ እንዳሉት በተቋሙ አገልግሎት አሰጣጥ ዉስንነት ጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርፕራይዞች ተገቢ የሆነ አገልግሎት በመስጠት ተጠቃሚ መሆን እንዳልቻሉ ጠቁመዋል፡፡ በዞኑ ነባር የኤሌክትሪክ ገመድ ተሸካሚ ምሰሶዎች ያረጁ በመሆናቸው እየወደቁ በህይወትና ንብረት ላይ አደጋ እያደረሱ እንደሚገኝ ለዲስትሪክቱ ቢገለጽም መፍትሄ እንዳልተሰጠዉ ጠቁመዉ ለኃይል መቆራረጥ መንስኤ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡ ህብረሰቡ አገልግሎት ለማግኘት ከአመታት በፊት ክፍያ ፈጽሞ ባለማግኘቱ የመልካም አስተዳደር ችግር በማድረግ ጥያቄ እያስነሳ በመሆኑ አፋጣኝ መፍትሄ እንዲሰጠዉም አቶ ታደለ ጠይቀዋል፡፡ ተቋሙ ለህብረተሰብ ተጠቃሚነት ቅርበት ያልተማከለ አሰራር መተግበሩ ለአገልግሎት አሰጣጥ የተሻለ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ በሀድያ ዞን የመልካም አስተዳደር ጉዳዮች ጽህፈት ቤት ኃላፊዉ አቶ ኦሰቦ ካለቲሶ ናቸዉ፡፡ የተቋሙ ሰራተኞች ከስነ ምግባር አንጻር የሚስተዋሉ ችግሮች እንዳሉባቸዉ በመጠቆም ከአርሶ አደሩ ከፍተኛ ገንዘብ የሚጠይቁ እንዳሉም ገልጸዋል። የቆጣሪ አቅርቦት እና ስርጭት እናደርጋለን በሚል የተለያዩ ስራዎችን የሚያከናዉኑ ሰራተኞችን ተቋሙ ከኅብረተሰቡ ጋር በቅንጅት በመስራት እርምጃ መዉሰድ እንዳለበት አሳስበዋል፡፡ የከንባታ ጠምባሮ ዞን ዉሃ ማዕድንና ኢነርጂ መምሪያ ኃላፊ አቶ ያዕቆብ ጎዴቦ በበኩላቸዉ በማዕከል ያሉ ባለ ሙያዎች የግብአት እጥረት እንዳለ በመግለጽ ተገቢዉን አገልግሎት አይሰጡም። ግብአቱ እያለም የእጅ መንሻ ካልተሰጠ አገልግሎት ለመስጠት ፍቃደኛ ባለመሆናቸዉ ህብረተሰቡ ለችግር እየተዳረገ መሆኑን አስታዉቀዋል፡፡ ከኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት ውስን መሆን ጋር ተያይዞ በሚፈለገው ልክ ንፁህ ውሃ ማቅረብ ባለመቻሉ ህብረተሰቡ የወንዝ ዉሃ ለመጠቀም መገደዱንም ተናግረዋል፡፡ በዞኑ ያሉ ኢንዱስትሪዎችም ተገቢ የሆነ አገልግሎት አግኝተው ተጠቃሚ መሆን እንዳልቻሉ በመጠቆም አፋጣኝ መፍትሄ ሊሰጠው እንደሚገባም ጠቁመዋል፡፡ በደቡብ ክልል ኤሌክትሪክ አግልግሎት የፕላንና ዲዛይን ስራ ሂደት ባለቤት አቶ አበበ እድሉ እንዳሉት የተነሱ ችግሮችን ለመቅረፍ ተቋሙ ትኩረት ሰጥቶ ይሰራል። ኃላፊነታቸዉን የማይወጡ አካላትን አጋልጦ በመስጠት ህብረተሰቡ ትብብር ሊያደርግ እንደሚገባም አስታዉቀዋል፡፡ “የተቋሙ ገቢና ወጪ ያልተመጣጠነ መሆን እና የግብአት አቅርቦት ዉስንነት መኖር የኃይል አቅርቦቱ ላይ እክል መፍጠሩን በመጠቆም ለችግሩ መፍትሄ ለመስጠት ዲስትሪክቱ እየሰራ እንደሚገኝ የተናገሩት የሆሳዕና ዲስትሪክት ስራ አስኪያጅ አቶ ዘመኑ ዳንኤል ናቸዉ፡፡ በ90 ከተሞች ያረጁ መስመሮችን ለመቀየር ታቅዶ እየተሰራ መሆኑንና ከኪራይ ሰብሳቢነት ጋር ተያይዞ ለሚነሱ ቅሬታዎች መፍትሄ ለመስጠት መረጃ ከቀረበ እርምጃ እንደሚወሰድም አስታዉቀዋል፡፡ የኤሊክትሪክ አገልግሎትን ተደራሽ ለማድረግ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር እየተሰራ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡    
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም