”የዩኒቨርሲቲዎች ጥምረት - ለስጋና ወተት እድገት” - ኢዜአ አማርኛ
”የዩኒቨርሲቲዎች ጥምረት - ለስጋና ወተት እድገት”
በምናሴ ያደሳ(ኢዜአ) የደቡብ ምዕራብ የአገሪቱ ክፍል በአብዛኛው በተፈጥሮ ደን የተሸፈነና ክረምት ከበጋ የሚፈሱ ትላልቅ ወንዞችና ጅረቶች በብዛት የሚገኙበት አካባቢ ነው::
ይህንኑ የተፈጥሮ ሀብት ተከትሎም በአለም አቀፍ ደረጃ ተመራጭ የሆኑ የተፈጥሮ ቡና : ማርና የቅመማ ቅመም ሰብሎች በቀላሉ ማልማት ይቻላል ።
ይኽው በተፈጥሮ ይዘቱ የታደለ አካባቢ እንደ ሀብት መጠኑ ለአገሪቱ ኢኮኖሚ ተገቢውን አስተዋፅኦ እያበረከተ አለመሆኑ ደግሞ ቁጭት ማስከተሉ አልቀረም ።
በተለይ ከላይ ከተጠቀሱት እምቅ ሀብቶቹ በተጨማሪ የእንስሳት መኖ ክረምት ከበጋ እንደ ልብ የሚገኝበትና የአየር ንብረቱም ለእንስሳት እርባታ አመቺ መሆኑ የብዙዎችን ቀልብ እየሳበ መጥቷል ።
እምቅ ሀብቱን ታሳቢ በማድረግም በቅርቡ አራት የመንግስት ዩኒቨርስቲዎች የአካባቢውን አመቺነት በመጠቀም የእንስሳት ልማት ፕሮጀክት በጋራ ለማከናወን የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርመዋል::
በመቱ ዩኒቨርስቲ በተዘጋጀው መድረክ ስምምነቱን የተፈራረሙት የመቱ: ወለጋ: አምቦና ጅማ ዩኒቨርስቲዎች ናቸው::
በዚሁ ጊዜ የፕሮጀክቱ አስተባባሪ ዶክተር ጌታቸው ተረፈ እንዳሉት ፕሮጀክቱ በአራቱ ዩኒቨርስቲዎች የጋራ ተሳትፎና በኦሮሚያ ክልላዊ መንግስትና በቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ሚኒስቴር ደጋፍ የሚከናወን ነው::
ፕሮጄክቱ በዋናነት የአካባቢውን ህብረተሰብ በማሳተፍ ለቀጣዮቹ አስር አመታት የሚከናወን ነው::
ዋና ዋና ተግባራቱም የአካባቢውን ነባር የቀንድ ከብት ዝርያ በተሻሻሉት መተካት ፣የእንስሳት እርባታ ፣ የመኖ ልማትና የስጋና ወተት ምርት ማቀነባበርያ ፋብሪካ ማቋቋም እንደሆነ አስተባባሪው ይናገራሉ።
የአካባቢውን አርሶአደሮችና ወጣቶች በባለቤትነት በማሳተፍ የስራ ዕድል መፍጠርና የኢኮኖሚ አቅማቸውን ማሳደግ አንዱ የትኩረት አቅጣጫ ነው ተብሏል ።
የልማት ፕሮጄክቱን በዚህ አመት በኢሉአባቦር ቡኖ በደሌና በምስራቅ ወለጋ ዞኖች ለመጀመር ሰባት የእንስሳት ልማት ጣቢያዎች ተቋቁመዋል::
ዶክተር ጌታቸው እንዳብራሩት በዚህ የእንስሳት ልማት ፕሮጀክት በ10 አመት ጊዜ ውስጥ ከ370 ሺህ በላይ የቀንድ ከብቶችን በማዳቀል ዝርያቸውን ለማሰሻሻል ታቅዷል ።
ይህም በአሁኑ ወቅት ከአንድ ላም የሚገኘውን 2 ሊትር ወተት ወደ 12 ሊትር ለማሳደግ ያስችላል::በልማት ፕሮጀክቱ ንድፍ መሰረት አርሶአደሮችና ወጣቶች በቀጥታ ተሳታፊ ይሆናሉ።
አርሶ አደሩ እንስሳቱን በተሻሻለ ዝርያ ካዳቀለ በኋላ ለእርባታ ጣቢያው በማስረከብ ከሚገኘው የስጋና ወተት ምርት እንደ አስተዋፅኦው መጠን ገቢ ያገኛል::
አርሶአደሩ እንስሳቱን በዘመናዊ መልኩ ለሚያከናወነው የእርባታ ጣቢያ ማስረከቡ በርካታ ጠቀሜታዎች እንደሚኖሩት ዶክተር ጌታቸው ይጠቅሳሉ::
ይህም በኋላ ቀር አረባብ የሚደርሰውን የእንስሳት ሞት መጠን በመቀነስ እንዲሁም ለመኖ ፍለጋ እንስሳቱን ራቅ ወዳሉ አካባቢዎች በማሰማራት ሲያጠፋ የነበረውን ጊዜና ጉልበት ለሌሎች የልማት ስራዎች እንዲያውል ይጠቅመዋል::
ወጣቶችም በማህበር በመደራጀት ለመኖ ልማት በተመረጡ አካባቢዎች የእንስሳት መኖ በማልማትና በማዘጋጀት ለእርባታ ጣቢያው እንዲያቀርቡ ማድረግ የፕሮጀክቱ አንዱ የትኩረት አቅጣጫ ነው::
ከ40 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ወጣቶች ስልጠና በመስጠትና ቁሳቁስ በማቅረብ የስራ ዕድል እንደሚፈጠርላቸው ነው የተጠቀሰው::
በፕሮጀክቱ ከታቀፉት ተግባራት መካከል የእንስሳት ጤና መጠበቅና መከላከል ስራዎችም ይገኙበታል:: በተሻሻሉ ዝርያ ከመተካት ባለፈ በእርባታው ለሚታቀፉና ለሌሎች የአካባቢው እንስሳት የክትባትና የህክምና አገልግሎት መስጠትም ያካትታል ።
ከእንስሳቱ የሚገኘውን የስጋና ወተት ምርት በማቀነባበርና እሴት በመጨመር ለአገር ውስጥ ገበያ ለማቅረብ የወተትና ስጋ ምርት ማቀነባበርያ ፋብሪካ ማቋቋም ሌላኛው ተግባር መሆኑን ዶክተር ጌታቸው ገልፀዋል::
ለዚህ የልማት ፕሮጀክት አንድ ቢሊዮን ብር በጀት የሚያስፈልግ ሲሆን የአጠቃላይ ወጪውን 60 ከመቶ በአራቱ ዩኒቨርሲቲዎች ይሸፈናል:: ቀሪው ደግሞ በኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት ድጋፍ የሚሟላ ይሆናል ።
የቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ሚኒስቴር ሚንስትር ዴኤታ አቶ ጀማል በክሪ እንዳሉት ፕሮጄክቱ ከዚህ ቀደም ከመቐለ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር በትግራይ ክልል ተጀምሮ ውጤታማ ሆኗል::
ይህንን ልምድ በመቀመርም በምዕራብ የአገሪቱ አካባቢዎች ለማስፋፋት ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ በትኩረት ይሰራል ብለዋል::
የምዕራብ የአገሪቱ ክፍል በተፈጥሮ ሀብት የበለፀገና ለመኖ ልማትና ለእንስሳት እርባታ ምቹ መሆን የአካባቢውን አርሶ አደሮች በከፍተኛ ደረጃ ተጠቃሚ የሚያደርግ እንደሆነም ጠቅሰዋል::
ፕሮጀክቱ የወተት ምርትን በስድስት እጥፍ ፣ የስጋ ምርት ደግሞ በሁለት እጥፍ የሚያሳድግ በመሆኑ ከአካባቢው ባለፈ የሀገር ውስጥ የገበያም ፍላጎት ማሟላት እንደሚችል ተናግረዋል::
የመቱ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶክተር እንደገና አበበ በበኩላቸው የመቱ ዩኒቨርስቲ ፕሮጀክቱን ለማስተባበር መመረጡ በማህበረሰብ አገልግሎት መስኮች ለሚያከናውናቸው ሌሎች ተግባራት ጭምር የበለጠ አቅም እንዲፈጥር ያደርገዋል::
ፕሮጄክቱ በተቀመጠለት ዓላማ መሰረት በአጭር ጊዜ ውጤታማ እንዲሆን ዩኒቨርሲቲው ሙሉ ዝግጅት ማድረጉን ነው የተናገሩት::
የቡኖ በደሌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሻፊ ሁሴን እንዳሉት በፕሮጀክቱ ለሚከናወኑ የእንስሳት እርባታና መኖ ልማት የሚሆን አመቺ ቦታ በማቅረብ አስተዳደሩ የበኩሉን ይወጣል::
ለልማት ስራው ስኬትም አስፈላጊ በሆኑ መስኮች ሁሉ ተገቢውን ድጋፍና ክትትል እንደሚደረግ ተናግረዋል::
የልማት ፕሮጀክቱ የአርሶአደሩን የኢኮኖሚ አቅም ከማሳደግ ባለፈ የወጣቶችን የስራ ዕድል ለመፍጠር ታሳቢ ተደርጎ መቀረፁ የአካባቢውን ልማት እንደሚያፋጥነው የተናገሩት ደግሞ የኢሉአባቦር ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ግርማ ረጋሳ ናቸው::
ዩኒቨርሲቲዎቹ ለጀመሩት ተስፋ ሰጪ የልማት ፕሮጀክት የዞኑ አስተዳደር ድጋፍ እንደማይለያቸውና በጋራ እንደሚሰራም ተናግረዋል::
መረጃዎች እንደሚያሳዩት በተፈጥሮ ሀብት በበለፀገው የደቡብ ምዕራብ አካባቢ አንድ ሚሊዮን የሚጠጉ የቀንድ ከብቶች ይገኛሉ።