የሲዳማ በክልል የመደራጀት ህዝበ ውሳኔ የመራጮች ምዝገባ ሠላማዊ ሂደትን ተከትሎ እየተካሄ ነው

61
(ኢዜአ) ህዳር 30ቀን 2012  የሲዳማ በክልል የመደራጀት ህዝበ ውሳኔ የመራጮች ምዝገባ ሠላማዊ ሂደትን ተከትሎ እየተካሄ መሆኑን የሃዋሳ ከተማ ተመዝጋቢዎችና የምርጫ አስፈጻሚዎች ተናገሩ። በከተማዋ ምዝገባ እየተከናወነባቸው ካሉ ጣቢያዎች መካከል ርኆቦት የምርጫ ጣቢያ አንዱ ነው ፡፡ በዚህ ጣቢያ የተመዘገበው ወጣት ዘላለም አለሙ በከተማዋ የህዝበ ውሳኔ የመራጮች ምዝገ ሂደት በሠላማዊ መንገድ እየተካሄደ ስለመሆኑ መመልከቱን ተናግሯል ፡፡ የነዋሪነት መታወቂያ ወደወሰደበት ቀበሌ በመሄድ በኆቦት ምርጫ ጣቢያ ምዝገባውን በሰላማዊ መንገድ ማካሄዱን ተናግሯል። በቀጣይም የህዝበ ውሳኔው ሂደት በሠላም ተካሂዶ እንዲጠናቀቅ ወጣቶች የአካባቢያቸውን ሠላም ማስጠበቅ እንዳለባቸው የገለጸው ወጣቱ "ውጤቱ ምንም ይሁን ምን በፀጋ ለመቀበል ዝግጁ ነኝ" ብሏል ፡፡ የርኆቦት ምርጫ ጣቢያ የህዝብ ታዛቢ አቶ አሰፋ አዴላ ተመዝጋቢዎች የታደሰ መታወቂ ይዘው በመቅረብ አሊያም ሌላ ማንነታቸውን የሚገልጽ ሕጋዊ ካርድ ወይም ወረቀት በማሳየት ተመዝግበው የመራጭ ካርድ እየወሰዱ መሆናቸውን ተናግረዋል። ከእዚህ በተጨማሪ መታወቂያ የሌላቸውን ከስድስት ወር በላይ በቀበሌው ስለመኖራቸው በህዝብ ታዛቢዎች በማረጋገጥ እንዲመዘገቡ እየተደረገ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ የምዝገ ሂደቱ ሠላማዊ እንደሆነ የተናገሩት አቶ አሰፋ አንዲት ዕድሜዋ 18 ዓመት ያልሞላት ልጅ ለመመዝገብ መምጣቷንና በወቅቱ እንደማትችል ተነግሯት መመለሷን አመልክተዋል፡፡ ባለፉት ሦስት ቀናት በጣቢያው 625 ድምጽ ሰጪዎች መመዝገባቸውን የገለፁት የእዚሁ ጣቢያ ኃላፊ ወይዘሪት ራህመት ሳኒ፣ እስካሁን ምንም አይነት ችግር እንዳላጋጠማቸው ተናግረዋል ፡፡ በከተማው የየሺ ምርጫ ጣቢያ ኃላፊ ወይዘሪት ሄለን ንጉሱ በበኩለቸው ሥራቸውን ያለ ምንም እንከን እያከናወኑ መሆኑንና እስካሁን 274 ተመዝጋቢዎችን ማስተናገዳቸውን አስረድተዋል ፡፡ የታደሰ መተወቂያ ይዘው በመምጣት መመዝገባቸውንና በምዝገባ ሂደት ያስተዋሉት ችግር አለመኖሩን የገለጹት ደግሞ የእዚሁ ጣቢያ ተመዝጋቢ ወይዘሮ አሽረቃ አብዱልቃድር ናቸው፡፡ ሠላማዊ ሂደቱ ከድምጽ መሰጫ ዕለት በፊትም ሆነ ከዚያ በኋላ ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደፈሚገባው ነው የገለጹት፡፡    
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም