የሕግ የበላይነትን ለማረጋገጥና አጥፊዎች በሕግ ፊት ቀርበው ተገቢው ሁሉ እንዲያገኙ ያለማወላወል እንሠራለን:- ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ

87
ጥቅምት 15/2012 የሕግ የበላይነትን ለማረጋገጥና አጥፊዎች በሕግ ፊት ቀርበው ተገቢው ሁሉ እንዲያገኙ ያለማወላወል እንሠራለን ሲሉ  ጠቅላይ ሚንስትር ዶክተር አቢይ  አህመድ ገለጹ። ጠቅላይ ሚንስትር ዶ/ር አቢይ በወቅታዊ ሀገራዊ ጉዳይ ላይ የሰጡት ሙሉ መግለጫ፡- የተከበራችሁ የሀገሬ ሕዝቦች! ሰሞኑን በተከሠተው እጅግ አሳዛኝ ግጭት በዜጎቻችንና በንብረታቸው ላይ በደረሰው ሁሉ ማዘኔን አስቀድሜ ለመግለጥ እወዳለሁ፡፡ ያጋጠመን ፈተና ኢትዮጵያውያን ካልተባበርንና አንድ ሆነን ካልቆምን መንገዳችን ምን ያህል አስቸጋሪና አስፈሪ ሊሆን እንደሚችል ማሳያ ነው፡፡ ችግሩ የብሔርና የሃይማኖት መልክ እንዲኖረው ለማድረግ ተሞክሯል፡፡ በዚህም የተነሣ ወገኖቻችን በአሰቃቂ ሁኔታ መሥዋዕት ሆነዋል፡፡ የጸሎት ቤቶች ተቃጥለዋል፡፡ የንግድ ድርጅቶችና የመኖሪያ ቤቶች ወድመዋል፡፡ የተፈናቀሉ ወገኖች በተለያዩ ቦታዎች ተጠልለዋል፡፡ መተላለፊያ ያጡ ዜጎችም በየከተሞቹ ከርመዋል፡፡ እንኳንስ ለማየት ለመስማት የሚዘገንን እኩይ ተግባር በወገናችን ላይ ተፈጽሟል፡፡ በልብ ሰባሪው ክሥተት ብናዝንም ኢትዮጵያውያን ዛሬም ታላቅ ሕዝቦች፣ አስተዋዮችና አመዛዛኞች መሆናቸውንም አይተናል፡፡ ቤተ ክርስቲያን እንዳይቃጠል የሚከላከሉ ሙስሊሞች፣ መስጊድ እንዳይቃጠል ዘብ የሚቆሙ ክርስቲያኖች አሉን፡፡ ከእነርሱ ብሔር ውጭ ለሆነው ወገናቸው ሲሉ መሥዋዕትነት የከፈሉ ኢትዮጵያውያን አሉን፡፡ ሰላምና ደኅንነትን ለማውረድ ሌት ተቀን የሚደክሙ ሽማግሌዎች አሉን፡፡ ቤት ንብረታቸውን ላጡ መጠለያ የሚሆኑ፣ መንገድ ለተዘጋባቸው ማደሪያ የሚያዘጋጁ ብዙ ወገኖች አሉን፡፡ የፈተናው ዓላማ ተስፋ እንድንቆርጥና መንገዳችንን እንድንቀይር መሆኑን ተረድተው፣ ዛሬ በሆነው ነገር ሳይደናገጡ፣ ነገን አሻግረው የሚመለከቱ ዜጎች አሉን፡፡ ለሕግና ለኅሊና የሚቆሙ የመከላከያና የፖሊስ አባላት አሉን፡፡ ይህ ሁሉ ለምን እንደመጣብን እናውቃለን፡፡ ከዚህ የበለጠ ፈተና ቢያጋጥመንም እንኳን የጀመርነውን ጉዞ አናቋርጥም፡፡ አረሙን እየነቀልን፤ ስንዴውን እየተከባከብን እንሄዳለን እንጂ ለአረሙ ስንል ስንዴውን አንተወውም፡፡ በመንገዳችን የሚያጋጥመንን ዕንቅፋት እያነሣን መንገዳችንን እንቀጥላለን እንጂ ወደ ቀኝም ወደ ግራም ወለም ዘለም አንልም፡፡ ፈታኞቻችን ያልተገነዘቡት ነገር ቢኖር የተከፈለውን መሥዋዕትነት ሁሉ ከፍለን የኢትዮጵያና የሕዝቦቿን ብልጽግና የምናረጋግጥ መሆናችንን ነው፡፡ የሕግ የበላይነትን ለማረጋገጥና አጥፊዎች በሕግ ፊት ቀርበው ተገቢው ሁሉ እንዲያገኙ ያለማወላወል እንሠራለን፡፡ በተፈጠረው አሳዛኝ ክሥተት የተጎዱት እንዲያገግሙ፤ ከቤት ንብረታቸው የተፈናቀሉት እንዲመለሱ፣ ንብረታቸው የጠፋባቸው እንደገና እንዲቋቋሙ ከሕዝባችን ጋር ሆነን በጽናት እንሠራለን፡፡ ይህንን ለማሳካትም የሃይማኖት ተቋማት፣ የሲቪክ ማኅበራትና መላው ሕዝብ ከጎናችን እንዲቆም ጥሪ እናደርጋለን፡፡ እርስ በርሳችን ከተከፋፈልንና ከተጋጨን አሸናፊዎቹ ሌሎች ናቸው፡፡ ማናችንም አናሸንፍም፡፡ ጠላቶቻችን ምን እንድንሆን እንደሚፈልጉ በጥቂቱ አይተነዋል፡፡ ከዚህ የከፋ እንዳይገጥመን መንግሥትና ሕዝብ የሚጠበቅባቸውን ማድረግ አለባቸው፡፡ መንግሥት ከመንግሥት የሚጠበቀውን ሁሉ ያደርጋል፡፡ ሕዝቡም ባለመለያየት፣ ለአጥፊዎች አጀንዳ ባለመመቻቸት፣ አንዱ ለሌላው ጋሻና መከታ በመሆን፤ ወንጀለኞችን አሳልፎ ለሕግ በመስጠት፣ የተጎዱ ወገኖቹን በመርዳት ታላቅነቱን ሊያስመሰክር ይገባል፡፡ ኢትዮጵያ በልጆቿ ጥረት ታፍራ፣ ተከብራና በልጽጋ ለዘላለም ትኑር! ፈጣሪ ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ! ጥቅምት 15 ቀን 2012 ዓ.ም
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም