የሩዋንዳ ብሔራዊ የእግር ኳስ ልኡካን ቡድን መቀሌ ገባ

57
መቀሌ ኢዜአ መስከረም 9/2012 የሩዋንዳ ብሔራዊ የእግር ኳስ ልዑካን ቡድን ዛሬ መቀሌ ከተማ ገባ። ልዑካን ቡድኑ መቀሌ ከተማ የገባው በሀገሪቱ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ምክትል ፕሬዝዳንት በመመራት ነው። መቀሌ አሉላ አባነጋ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ሲደርስ በትግራይ ክልል ወጣቶችና ስፖርት ጉዳይ ቢሮ ተወካይ አቶ ካህሳይ ፍሰሃና በክልሉ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አንገሶም ካህሳይ  አቀባበል ተደርጎለታል ። የቡድኑ አባላት ወደ ተዘጋጀላቸው ማረፊያ በደረሱበት ወቅትም በመቀሌ ስፖርት ደጋፊዎች  ደማቅ አቀባበል ተደርጎላቸዋል ። የሩዋንዳ ብሔራዊ የእግር ኳስ ቡድን መቀሌ የገባው ከኢትዮጵያ አቻው ጋር ለሚያደርገው የቻን ውድድር ነው። ሁለቱ ቡድኖች የቻን ማጣሪያ ውድድራቸውን በመጪው እሁድ ከቀኑ አስር ሰዓትጀምሮ  በትግራይ ዓለም አቀፍ ስታዲዮም እንደሚያካሂዱ ታውቋል ። የሩዋንዳ ብሄራዊ እግር ኳስ ቡድን ነገ  በስታዲዮሙ  ተገኝቶ ልምምድ እንደሚያደርግ ተመልክቷል። ስድስተኛው የአፍሪካ ሀገሮች የቻን እግር ኳስ ውድድር  በጥር ወር 2012 ዓ.ም በካሜሮን አስተናጋጅነት ይካሄዳል።  
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም