ያልተገራው ሀብት - ካቲካላ

317

ገብረህይወት ካህሳይ /ኢዜአ/

አቶ ዘውዱ አስፈራቸው የአርሲ ነገሌ ከተማ ነዋሪ ናቸው። ኑሮአቸውን የመሰረቱት በባህላዊ መንገድ የሚመረተውን የአበሻ አረቄ በመቅመስና በመሸጥ መሆኑን ይገልጻሉ።

“አገር በቀል እውቀት” በባህላዊ መንገድ የሚመረተው የአበሻ አረቄ (ካቲካላ) ተብሎ የሚታወቀውን የአልኮል መጠጥ ለገበያ በማቅረብ 10 ዓመታትን አሳልፈዋል።

አቶ ዘውዱ አረቄ ነጋዴ ብቻ አይደሉም ። ከጀሪካን ውስጥ አረቄውን ወደ ጠርሙስ እየሳቡ በማውጣት ቀማሽ ‘ባለሙያ’ ጭምር መሆናቸውን ነው የሚናገሩት። በገበያው አነጋገር ሳቢና ቀማሽ ይባላሉ ።

ኢትዮጵያ ከምትታወቀባቸው የአገር በቀል እውቀት ሀብቶች ከሆኑት የምግብና የመጠጥ ውጤቶች መካከል የአረቄን “ባህላዊ ደረጃ” በቅምሻ በመለየትና በአቅራቢነት ላለፉት ዓመታት ኑሮአቸውን መርተውበታል ።

በአርሲ ነገሌ ልክ እንደእርሳቸው አረቄ በመቅመስና የገበያውን ዋጋ በመወሰን የሚተዳደሩ 300 ያህል ባለሙያዎች አሉ። እነዚህ “ባለሙያዎች” በሳምንቱ ውስጥ ልዩ የገበያ ቀናት በሆኑት ሰኞ ፣ ረቡዕና ዓርብ የሚቀርበውን አረቄ “ባህላዊ ደረጃና ዋጋ” ይወስናሉ።

ሽያጩ ሲካሄድ እንደ አቶ ዘውዱ ያሉ ቀማሾች የአረቄውን ጥራትና ጥንካሬ መወሰን ይጠበቅባቸዋል። እየቀመሱ በመትፋት ጥራቱ አንደኛ ነው፣ ሁለተኛ ደረጃ ነው እና ደካማ ነው ይላሉ።

አቶ ዘውዱ እንደሚሉት፤ የአረቄውን መልክ በማየትና በመቅመስ የጥራት መጠኑን ያውቁታል።

እርሳቸው የሚቀምሱት ወደ ውስጥ ሳያስገቡ ስለሚተፉት “በጤንነቴ ላይ ጉዳት ያስከተለበት አጋጣሚ የለም” ይላሉ።

የእርሳቸውን ዓይነት ‘ባለሙያዎች’ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የገበያውን ዋጋ የመወሰን አቅም እንዳላቸው ነው አቶ ዘውዴ የሚናገሩት። ገበያው ለአካባቢው ህዝብ እንደ አንድ ትልቅ ፋብሪካ መተዳደሪያው መሆኑንም ያመለክታሉ።

በአርሲ ነገሌ ከገበያው በየቀኑ በአማካይ ከ20 እስከ 30 አይሱዙ የጭነት ተሽከርካሪዎች የአበሻ አረቄ ጭነው ወደ ሰሜን ፣ ደቡብና ምስራቅ የአገሪቷ ክፍሎችና ወደ አዲስ አበባ እንደሚጓጓዝ ነው አቶ ዘውዱ የሚናገሩት።

ሌላው አረቄ ቀማሽ “ባለሙያ” ወጣት ደጀኔ ወልደማርያም በሰጠው አስተያየት፤ በከተማዋ የሚቀርበውን አረቄ በመቅመስ ይተዳደራል።

የአረቄ ገበያው ከበፊቱ ጋር ሲነፃፀር በውሃ እጥረት ምክንያት መቀዛቀዝ ይታይበታል።

ከአካባቢው በፊት በቀን በአማካይ እስከ 20 መኪና አረቄ ተጭኖ ሲወጣ ነበር። አሁን ግን ቀንሶ ወደ 15 አይሱዙ ዝቅ ማለቱን ነው ወጣት ደጀኔ የሚናገረው ።

የአረቄ ሳቢዎችና ቀማሾች እለታዊ ገቢ እንደየደንበኞቻቸው ብዛትና የመግዛት አቅም ይለያየል ። ከዝቅተኛ ነጋዴዎች ጋር የሚሰሩ ሳቢና ቀማሾች በቀን አነሰ ቢባል 500 ብር ያገኛሉ ። ከትላልቅ ነጋዴዎች ጋር የሚሰሩና ብዛት ያለው አረቄ የሚቀምሱ ደግሞ እስከ 3 ሺህ ብር ድረስ ያገኛሉ ።

የአርሲ ነገሌ ከተማ አስተዳደርም ይህንኑ የሚያጠናክር አስተያየት ይሰጣል ። የከተማ አስተዳደሩ የገበያ ልማት የስራ ሒደት ዋና ሃላፊ አቶ ከድር ዋቆ ለኢዜአ እንደገለጹት በከተማዋ ሳምንቱን ሙሉ የአበሻ አረቄ ግብይት ይካሔዳል ።

አቶ ከድር እንደሚሉት ሰኞ ፣ ሮብና ዓርብ ዋነኞቹ የገበያ ቀናት ናቸው ። በሶስቱ ዋነኛ የአበሻ አረቄ የገበያ ቀናት በቀን በአማካይ 30 አይሱዙ የጭነት ተሽከርካሪዎች አረቄ ጭነው ወደ ተለያዩ አካባቢዎች ይጓዛሉ።

በሌሎቹ ቀናትም ቢሆን በአንፃራዊነት መጠኑ ይቀንስ እንደሆነ እንጂ በቀን ከ15 እስከ 20 አይሱዙ ተጭከርካሪ አረቄ ጭኖ ይወጣል ። ይህንኑም ከፍተኛ የገበያ ፍላጎትና የገንዘብ ዝውውር መኖሩን ይጠቁማል ።

አቶ ከድር እንደሚናገሩት የአበሻ አረቄውን የጥራት ደረጃና ዋጋ የሚወስኑ ቀማሾች በማህበር የተደራጁ፣ በነጋዴዎች የተመረጡና በገበያው ረጅም ጊዜ የሰሩ ናቸው።

የተቀመሰውን የአበሻ አረቄ ለአንድ ባለ 25 ሊትር ጀሪካን ከ150 እስከ 800 ብር የሚያወጣ ደረጃ ይሰጠዋል።

በአርሲ ነገሌ ከተማ “አረቄ የማይወጣበት ቤት የለም” ያሉት ዋና የስራ ሂደት ሃላፊው ምክንያቱ ደግሞ ከአበሻ አረቄው ከሚገኘው ገቢ ባሻገር አተላው ወይም ዝቃጩ ለእንስሳት መኖ አገልግሎት በማዋል ሌላ የገቢ ምንጭ ሆኖ ስለሚያገለገል ነው ።

የተለያዩ ሙሁራንና ተቋማት ያደረጉዋቸው ጥናቶች እንደሚያመለክቱት ዘርፉ በርካታ ኢትዮጵያዊያን የተሰማሩበትና ብዙ ሀብት የሚንቀሳቀስበት ነው ። በቅርቡ የተደረገ ጥናት እንደሚያመለክተውም በአርሲ ነገሌ አካባቢ በየአንዳንዱ ቤት በስድስት ቀናት ውስጥ 150 ሊትር አረቄ ይመረታል።

የራስወርቅ አድማሱ እና ኢዛናአ አምደወርቅ በ2010 በማህበራዊ ኢኮኖሚ አተያይ ባደረጉት ጥናት በአርሲ ነገሌ የገበያ ትስስር ውስጥ ቀማሾች፣ አሻሻጮች፣ የገበያ ዋጋ ተደራዳሪዎች ከፍተኛ ድርሻ አላቸው።

እነዚህ የገበያ ትስስሮች የብዙ ሰዎችን ኑሮ ለመምራት የሚያስችሉ ናቸው ። በጥናቱ ግኝት ላይ እንደተጠቀሰው ከሆነ በአርሲ ነገሌ የአረቄ ገበያ የሚገኙ የጠባቂዎችና ደላሎች ማህበራት ከሚያገኙት ገቢ ረዳት የሌላቸው ልጆችን ይደግፋል ። ትምህርታቸውን እንዲከታተሉም ያደርጋል።

ባህርዳር ዩኒቨርስቲ እ.ኤ.አ በ2012 ባዘጋጀው ሲምፖዚየም ላይ የቀረበ ጥናት እንደሚያመለክተው ደግሞ በአገር በቀል እውቀት የሚመረቱት አብዛኛዎቹ ምግብና መጠጦች በርካታ ሰዎች ኑሮዋቸውን ለመምራት የሚያስችላቸው ገቢ ያስገኝላቸዋል። ከዚህ በሚያገኙት ገቢም ልጆቻቸውን ያሰተምሩበታል።

የኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት የአምቦ ግብርና ምርምር ማዕከል ተመራማሪ ታሪኩ ሁንዱማ ይህንኑ ጥናት ምንጭ ጠቅሰው እንደገለጹት በአርሲ ነገሌ ከተማ ብቻ 87 ነጥብ 3 በመቶ የሚሆኑት በአረቄ ገበያው ቀጥተኛ ተጠቃሚዎች ናቸው ።

የምግብ፣ መጠጥና ፋርማሲዩቲካል ኢንዱስትሪ ልማት ኢንስቲትዩት የመጠጥ ፕሮሰሲንግ ዳይሬክተር አቶ አክሊሉ ከፍያለው እንደሚሉት በባህላዊ መንገድ የሚወጡት አረቄና ሌሎች መጠጦች ለበርካታ ሰዎች የኑሮ ዋስትና ሆነው ዘልቀዋል ። ይህ ባህላዊ መጠጥ በተሻለ መንገድ ቢመረትና ታሽጎ ቢወጣ የተሻለ ጠቀሜታ ይኖረዋል ። የውጭ ምንዛሪ ምንጭ ሆኖም ሊያገለግል ይችላል ።

ነገር ግን እስከ አሁን ድረስ ተገቢው ክትትልና ድጋፍ አይደረግለትም ። ምክንያቱ ደግሞ የሰው ሃይልና የቴክኖሎጂ ሽግግር እጥረት ነው ተብሏል ።

በደብረ ብርሃን፣ በሰላሌና በተለያዩ የአገሪቷ ክፍሎች ለብዙዎች የስራ እድል የፈጠረው የአገር በቀል እውቀት ስራዎችን እውቅና ሰጥቶ በኢንተርፕርነርነት ደረጃ አደራጅቶ በንግድ ሰንሰለት በማካተትና በህጋዊ መንገድ ስራዎችን ለማከናወን የክትትልም ሆነ የድጋፍ ችግር መኖሩን ነው አስተያየት ሰጪዎች የሚያመለክቱት።

ዘርፉ ራሱን የቻለ ችግርም ይታይበታል ። አረቄው በክፍት ገበያ ለአቅመ አዳምና አቅመ ሔዋን ላልደረሱ ወጣቶች ጭምር ሃይ ባይ ሳይኖረው በየቦታው የሚቸበቸብ መሆኑ ነው ። ይህ ደግሞ አገሪቷ በቅርብ ካወጣችው ህግ ጋር ይቃረናል።

አርሲ ነገሌ ከተማን ጨምሮ ከዓመት ዓመት የማያቋርጥ ሰፊ የአበሻ አረቄ ግብይት እየተካሔደ ቢሆንም የፈጠረው የስራ ዕድል ፣ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታው ፣ በጤንነት ላይ ተፅእኖ ካለውና ከቀረጥ ለከተማው የሚያበረክተው ገቢ በተመለከተ የተካሄደ ጥናትና የተደራጀ መረጃ አለመኖሩን ከሃለፊዎቹ ማብራሪያ ለመረዳት ይቻላል።

ነገር ግን የምግብ፣ መጠጥና የፋርማሲዩቲካል ኢንዱስትሪ ልማት ኢንስቲትዩት የመጠጥ ፕሮሰሲንግ ዳይሬክተር አቶ አክሊሉ ከፍያለው እንደሚናገሩት ካቲካላ በተለያዩ አካባቢዎች በብዛት ይመረታል።

የአገር በቀል እውቀት ውጤት የሆኑት ምርቶች በገበያ ያላቸው ድርሻ፣ የገበያው ትስስር ታስቦ ወደ ተሻለ የአመራረት ደረጃ በማድረስ ማህበረሰቡን በማሳተፍ በተለይ ደግሞ ሴቶችን ተጠቃሚ ለማድረግ የሚያስችል ጥናት አልተደረገበትም ።

ከዩኒቨርስቲ ባሻገር የሚመለከታቸው የመንግስት ተቋማትየተጠናከረ ጥናት አለማካሔዳቸውና በኢንተርፕርነርሺፕ ተጠናክሮ በአገር ኢኮኖሚ ገንቢ ሚና እንዳይጫወት ማድረጉን ነው መረጃዎች የሚያመለክቱት።

አንዳንድ መረጃዎች እንደሚያሳዩት ቮድካና የአበሻ አረቄ የአልኮል ይዘታቸው ተቀራራቢ ነው ። የአበሻ አረቄ የአልኮል መጠኑ ከ45 እስከ 47 በመቶ ሲሆን ቮድካ ደግሞ በአውሮፓ መጠኑ ከ37 ነጥብ 5 እስከ 40 በመቶ ባለው ደረጃ ላይ የሚገኝ ነው ።

ቮድካ በዘመናዊ መንገድ እየተመረተና በስፋት ለገበያ የሚቀርብ ከሆነ የኛው የአበሻ አረቄም በዘመናዊ መንገድ እንዲመረት በማድረግ ለውጭ ገበያ የሚቀርብበት ፣ አምራቹ የተሻለ ዋጋ የሚያገኝበትና ስራው በጥናት ላይ ተመስርቶ የሚመራበት ሁኔታ ቢፈጠር መልካም ነው ።

አረቄውን በማውጣት ፣በመቅመስና በመጠጣት ሊመጣ የሚችል የጤና ስጋት ካለ ለመከላከል ይረዳ ዘንድም በልዩ ትኩረት ቢጠና ሳይሻል አይቀርም ። ከአገራዊ ህጉ ጋር እንዳይጋጭም ጥንቃቄን ያሻል ። ካልሆነ ግን የጥቅሙን ያክል የጎንዮሽ ጉዳት ሊኖረው ይችላል ።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም