በአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር የተመራ የሉዑካን ቡድን ሰቆጣ ከተማ ገባ

144
ነሀሴ 15 ቀን 2011 (ኢዜአ)  በአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ተመስገን ጥሩነህ የተመራ የሉዑካን ቡድን ሰቆጣ ከተማ ገባ። የልዑካን ቡድኑ በዋግህምራ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን ሰቆጣ ከተማ የገባው ዛሬ ማምሻውን ነው። ቡድኑ በብሔረሰብ አስተዳደሩ በሚኖረው ቆይታ በነገው ዕለት በከተማው በሚከበረው የሻደይ በዓል ላይ እንደሚታደም ታውቋል። ከበዓሉ ጎን ለጎን ከዞኑ ከተውጣጡ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ጋር ልማትና መልካም አስተዳደርን አስመልክቶ ውይይት ያደርጋል ተብሎ ይጠበቃል። ርዕሰ መስተዳድሩ በሦስት ቀን ቆይታቸው ዞኑን ከደቡብ ጎንደር እንዲያገናኝ ታስቦ የተገነባውን የአምደወርቅ - ተከዜ የ48 ኪሎ ሜትር የጠጠር መንገድ እንደሚመርቁ ታውቋል። በሻለቃ አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ የተገነባውን የገልኩ 1ኛ ደረጃ ትምህርት ቤትንም ርዕሰ መስተዳድሩ ይመርቃሉ ተብሎ ይጠበቃል። የልዑካን ቡድኑ ውስጥ የአማራ ክልል ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ወርቅ ሰሙ፣ የአዴፓ ማዕከላዊ ኮሜቴ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ዮሐንስ ቧያለው እንዲሁም ሌሎች የክልሉ የሥራ ኃላፊዎች የተካተቱበት መሆኑ ታውቋል ።    
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም