ለትውልድ የሚተርፍ አሻራ - ኢዜአ አማርኛ
ለትውልድ የሚተርፍ አሻራ

በሃብታሙ አክሊሉ (ኢዜአ) የዛፍ መትከል ባህል ጥንትም የነበረ ልማድ መሆኑን የታሪክ ድረሳናት ያስረዳሉ። ጥንታውያን ግሪኮችና ሮማውያን ዛፍ መትከል ሰፊ ልማድ እንደነበራቸው ይነገራል። ሮማውያኑ በጥንተ ዘመናቸው የነበራቸውን የችግኝ አተካከል ጥበብ በመዛግብት አኑረውት ለዚህኛው ትውልድ አስተላልፈውታል። የችግኝ መትከያ ጉድጓዶች አቆፋፈር፣ የተክሎች ስር አጠባበቅ፣ የዛፍ ችግኞችን በቀለማት የመለየት ዘዴን፣ የሚተከሉ ችግኞች ከፀሃይና ከንፋስ ጋር የሚኖራቸውን ዝምድና እና ሌሎች ዘዴዎችን ሮማውያኑ ለአሁኑ ትውልድ አሻግረዋል። በተጨማሪም ሮማውያኑ የተለያዩ ፍራፍሬዎችን ወደ ብሪታኒያ እንዳመጡም ታሪክ ይመሰክርላቸዋል። ሮማውያኑ የአትክልተኛነት ጥበብን የተካኑ እንደነበሩም ድርሳናቱ ያስረዳሉ። በጥንታዊ ስልጣኔ ውስጥ ያለፈችው ሃገራችንም ከግሪክ እና ሮማውያኑ ባልተናነሰ ሃገር በቀል የዛፍ ዝርያዎችን ጠብቆ ከማቆየት ጋር የተዛመደ ታሪክ አላት። አጤ ምኒሊክ በዘመነ መንግስታቸው ወቅት የባህር ዛፍ ዝርያዎችን ከአውስትራሊያ በማስመጣት በተለያዩ የሃገሪቱ ክፍሎች እንዲተከሉ የማድረጋቸው ታሪክ ከችግኝ ተከላ የዘመቻ መርሃ ግብር ጋር ተያይዞ ሊነሳ የሚችል በ1886 ዓ.ም የተከወነ ታሪክ ነው። የባህር ዛፍ የሚለው ስያሜንም ዛፉ ከባህር ማዶ ወደ ሃገር ቤት ከመግባቱ ጋር ተያይዞ እንዳገኘ ታሪክ ይነግረናል። ምኒሊክ የዛፉ ችግኝ ተፈልቶ ለአቅመ መተከል ከደረሰ በኋላ ህዝቡ ችግኙን እየወሰደ እንዲተክል በማሰብ “የባህር ዛፍ የተተከለበትን መሬት ግብሩን ምሬያለሁ” የሚል አዋጅ አውጥተው ህዝቡ በሽሚያ የዛፍ ችግኞችን እየወሰደ መትከል መጀመሩና በጊዜው ችግኙ ተወዶ አርባ ችግኝ በአንድ ጥሬ ብር እንደተሸጠ ዻውሎስ ኞኞ አጤ ምኒሊክ በሚለው መፅሃፉ ላይ ከትቦታል። ሃገራችን ችግኝ አፍልቶ ዛፍ የመትከልን ታሪክ በ19ኛው ክፍለ ዘመን መባቻ ላይ ባህል ብታደርግም የተለያዩ ሃገር በቀል ዛፎችን ጠብቆ የማቆየት ከመቶዎች አመታት የተሻገረ ልማድ አላት። በአብያተ ክርስቲያናት፣ በጥንታዊ መስኪዶች እና በነገስታት አፀድ የሚገኙ ዕድሜ ጠገብ ዛፎችን መመልከቱም ለዚህ ሃቅ ምስክር ሊሆን ይችላል። ከዚያም በኋላ በየጊዜው የመጡ የመንግስት አስተዳደሮች የተለያዩ መርሃ ግብሮችን በመንደፍ የችግኝ ተከላ ተግባሩን ሲፈፅሙት ቆይተዋል። በአፄ ሃይለስላሴ፣ በደርግ እንዲሁም በኢህአዴግ የስልጣን ዘመናት በተለያዩ መሪ መልዕክቶች ሰፋ ያሉ የችግኝ ተከላ ዘመቻዎች ተካሄደዋል። ከሃገራችን የቆዳ ስፋት 40 በመቶ የሚሆነው ክፍል በደን የተሸፈነ እንደነበር በታሪክ የምናውቀው ሃቅ ቢሆንም ይህ አሃዝ ወደ ታች አሽቆልቁሎ 3 በመቶ ደርሶ እንደነበርም የቅርብ ጊዜ ትውስታ ነው። ከምዕተ አመቱ መግባት ጋር ተያይዞ 2000 ዓ.ም በተከናወነ የቅስቀሳ ስራ በዘመቻ በተካሄደው የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ወደ 3 በመቶ ወርዶ የነበረውን የሃገሪቱ የደን ሽፋን ወደ 15 በመቶ ከፍ እንዲል ተደርጓል። ይኸው የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር መዲናችንን የከበቡ ገላጣ ተራሮች መልሰው እንዲያገግሙ ማድረጉንም በጊዜው በየካ እና ሌሎች ጋራዎች ላይ የታየው ለውጥ ምስክር ነው። አሁን ደግሞ ኢትዮዽያ 4 ቢሊዮን የዛፍ ችግኞችን ለመትከል ውጥን ይዛ እንቅስቃሴ ከጀመረች እንሆ ወራት ተቆጠሩ። አንድ ግለሰብ 40 ችግኞችን የመትከል ዕቅድ ይዞ ተግባሩን እንዲወጣም ሃገሪቱ ሃላፊነቱን ሰጥታዋለች። በዚህ የዛፍ መትከል ዘመቻ 400 ሺ ሄክታር መሬት በዛፍ ለመሸፈን እንደታቀደ የግብርና ባለሙያዎች ተናግረዋል። ሃምሌ 22 ቀን 2011 ዓ.ም በአንድ ጀምበር 200 ሚሊዮን ችግኞችን የመትከል ትልም ተነድፎ የችግኝ ዝግጅትና የጉድጓድ ቁፋሮዎች ተከናውኗል። በዕለቱ ሁሉም ዜጋ የዜግነት ግዴታውን ለመወጣት ቀኑን በጉጉት እየጠበቀው ይገኛል። ይህንን የዛፍ መትከል መርሃ ግብር ከዚህ ቀደም ሲከናወን ከበነረው የሚለየው እንደየአካባቢው ሁኔታ ተስማሚ የሆኑ የዛፍ ችግኞች ፈልተው መሰናዳታቸው ነው። ስራው የበርካቶችን ድጋፍ ከማግኘቱም በዘለለ ከዚህ ቀደም ባልታየ ቅንጅት ለማከናወን መታሰቡም ለየት እንደሚያደርገው ተነግሯል። የሃገራችንን ከብዙ በጥቂቱ በዚህ መልኩ ከተመለከትን አህጉራዊና አለም አቀፍ የዛፍ መትከል ታሪኮች ምን ልምዶች ተቀምረውባቸዋል? ምንስ የሚነግሩን ጉዳይ አላቸው? እንመልከታቸው። በቅርቡ የጀርመኑ ዶቼ ቬሌ ‘The Man Greening Burkina Faso’s Desert’ በሚል ርዕስ የቡርኪና ፋሶ ዜጋን ጠንካራ የደን ልማት ታሪክን ያዘለ አስገራሚ መረጃን አሰራጭቷል። ያኩባ ሳዋዶጎ የተባለው ቡርኪናፋሶአዊ የ80 አመት አዛውንት እኤአ ከ1980 ዓ.ም ጀምሮ በሃገሩ በረሃማነትን ለመግታት በሚል አጋዥ ሳይኖረው ብቻውን የዛፍ መትከል ተግባሩን ይጀምራል። ከተጠቀሰው ጊዜ ጀምሮ የሳዋዶጎን ልፋት የጠየቀው የዛፍ መትከል ስራ እንሆ አሁን ፍሬ አፍርቶ ለአካባቢው ጥላን፣ ለመኖሪያው ጥሪትን አምጥቶለታል። ያኩባ ሳዋዶጎ የሚኖርባት ጎርካ የተባለችው መንደር አሁን የበረሃ ገነት ሆናለች። ለለምለሚቷ የሳዋዶጎ መንደር ምስጋና ይግባና የአካባቢው ነዋሪ ቢርበው ምግቡን፣ ጤናው ቢታወክ የባህል መድሃኒቱን ከዛፎቹ ያገኛል። ያኩባ ሳወዶጎም 27 ልጆቹን እና የልጅ ልጆቹን በምግብ እና በህክምና ይንከባከባል። ‘ጎርካ’ የተሰኘችው መንደርም የችግኝ አፈላል፣ አተካከልና እንክብካቤ ስልጠና የሚሰጥባት መንደር ሆናለች። ሳዋዶጎም በዚህ ተግባሩ የኖቤል ሽልማት ተሸላሚ ሊሆን ችሏል። እኤአ በ1870ዎቹ አካባቢ ስቴፈን ስሚዝ የተባለ አሜሪካዊ ሃኪም በኒውዮርክ ከተማ ዛፍ እንዲተከል ሰፊ ቅስቀሳ ማድረጉን መረጃዎች ይጠቁማሉ። እንደ መረጃዎቹም ስሚዝ በወቅቱ ሰዎች ዛፍ እንዲተክሉ ካነሳሳበት ጉዳይ አንዱ ከመጠን ያለፈ ሙቀት የሰው ልጆችን ህይወት ሊቀጥፍ እንደሚችል እና ዛፍ በመትከል ግን ተፅዕኖውን መቀነስ እንደሚቻል በማስተማር ነበር። ዛፎችን በመትከል ብቻ በሙቀት ሳቢያ የሚገጥመንን የጤና መታወክ ከመቀነሱም ባሻገር በአመት (ከያኔው አሃዝ አንፃር) ከ3ሺ እስከ 5ሺ የህፃናት ህይወትን መታደግ እንደሚቻል ስሚዝ አዘውትሮ ያስተምር ነበር። ከማስተማርም በዘለለ ስሚዝ የተለያዩ መፍትሄ አፍላቂ ጥናቶችን በማውጣት ለዘርፉ ባለሙያዎች እንዳበረከተም መረጃዎቹ አስረድተዋል። ልክ እንደ ያኩባ ሳዋዶጎ እና ስቴፈን ስሚዝ ያሉ በግለሰብ ደረጃ መሰል ተግባራትን የፈፀሙ ሰዎችን በሃገራችን ይገኛሉና ተግባራቸውን በማውጣት ሌሎች እንደ እነርሱ አይነት ሰዎች እንዲበዙ መስራት ይጠበቅብናል። ከርዕሰ ጉዳዩ ጋር በተያያዘም ‘ናሽናል ጂኦግራፊክ’ የዛፍ ችግኝን ጥቅም ላይ አውለው አለማችንን ያስደመሙ ሰዎች አምስት አጋጣሚዎችን በእትሙ ይዞ ወጥቷል፤ ቀጥለን እንመልከታቸው።
- ከ14 ቢሊዮን በላይ ዛፎችን የተከለው ታዳጊ
- ደን ፈጣሪው ህንዳዊ
- የፍራፍሬ ችግኞችን ለአሜሪካ ያስተዋወቀው ግለሰብ
- ለገና ዛፍ ህይወታቸውን አደጋ ላይ የጣሉ የአንድ መንደር ነዋሪዎች
- የለንደን ከተማን ግዙፍ የዕፅዋት ማዕከል ለማድረግ የተለመው ግለሰብ