ፍርድ ቤቱ አቶ ጌታቸው አሰፋን ጨምሮ ሌሎች ተጠርጣሪዎች ጉዳያቸው በሌሉበት እንዲታይ ትእዛዝ ሰጠ

73
አዲስ አበባ ኢዜአ ሀምሌ 9/2011የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት አቶ ጌታቸው አሰፋን ጨምሮ አራት ተጠርጣሪዎች ጉዳያቸው በሌሉበት እንዲታይ ትእዛዝ ሰጠ። ከከፍተኛ የሰብአዊ መብት ጥሰት ጋር በተያያዘ በወንጀል የተጠረጠሩት የቀድሞው የብሔራዊ መረጃና ደህንነት አራት ሃላፊዎች ጉዳያቸው በሌሉበት እንዲታይ የፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት አንደኛ ወንጀል ችሎት ዛሬ ትእዛዝ ሰጥቷል። በእነ አቶ ጌታቸው አሰፋ የክስ መዝገብ ውስጥ ከተከሰሱት 26 ተጠርጣሪዎች መካከል አቶ ጌታቸው አሰፋን ጨምሮ አራት ተጠርጣሪዎች ፖሊስ በመጥሪያ ሊያቀርባቸው አልቻለም። በመሆኑም ተጠርጣሪዎቹ በጋዜጣ ጥሪ ተደርጎላቸው እንዲቀርቡ በተሰጠው ትዕዛዝ መሰረት ሃምሌ 2 ቀን 2011 ዓ.ም በወጣው አዲስ ዘመን ጋዜጣ ለሃምሌ 8 ቀን 2011 ዓ.ም እንዲቀርቡ ቀጠሮ ጥሪ ተደርጎላቸው አለመቅረባቸው ተረጋግጧል። በመሆኑም ፍርድ ቤቱ ክሳቸው በሌሉበት እንዲታይ ትዕዛዝ ሰጥቷል። ሌሎች በዚሁ መዝገብ የተከሰሱ 22 ተከሳሾች በማረሚያ ቤት ሆነው ጉዳያቸውን እንዲከታተሉ የዋስትና መብት ውድቅ የተደረገባቸው መሆኑም ይታወሳል። ስለሆነም ከሐምሌ 18 ቀን 2011 ዓ.ም ጀምሮ ምስክርነት ለመስማት ፍርድ ቤቱ ቀጠሮ ሰጥቷል።        
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም