ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለሁለት የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች ሹመት ሰጡ

አዲስ አበባ ግንቦት 30/2010 ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ ዛሬ ለሁለት የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች ሹመት ሰጥተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሰጡት ሹመት ጄኔራል ሰዓረ መኮንን የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኤታማዦር አድርገው ሾመዋል። ጄኔራል አደም መሐመድን ደግሞ የብሔራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር አድርገዋል። የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት ለኢዜአ በላከው መግለጫ፤ ኃላፊዎቹ ከግንቦት 30 ቀን 2010 ዓ.ም ጀምሮ ሲሾሙ የአላቸውን ልምድ ከግምት ውስጥ መግባቱን አምልክቷል። ፕሬዚዳንት ዶክተር ሙላቱ ተሾመ በጥር 26 ቀን 2010 ዓ.ም ለመከላከያ ሰራዊት አባላት ወታደራዊ ማዕረጎችን በሰጡበት ወቅት ሌ/ጄኔራል ሰዓረ መኮንን ይመር እና  ሌ/ጄኔራል አደም መሐመድ የጄኔራልነት ማዕረግ መስጠታቸው ይታወሳል። አሁን የተሾሙት ጄኔራሎች ከዚህ በፊት በቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ በምክትል ጠቅላይ ኤታማዦር  ማዕረግ መሾማቸው ይታወቃል። ጄኔራል ሰዓረ መኮንን ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም የነበሩትንና ዛሬ የአገሪቷ እጅግ ከፍተኛ የኒሻን ሽልማት የተበረከተላቸውን ጄኔራል ሰሞራ የኑስን ተክተዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም