ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ ከሶማሊያ ፕሬዚዳንት ጋር ተወያዩ

122

አዲስ አበባ ግንቦት 25/2011 ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ የሶማሊያ ፕሬዚዳንት መሐመድ አብዱላሂ መሐመድንና ልዑካቸዉን በጽህፈት ቤታቸዉ አናግረዋል።

ፕሬዚዳንት መሓመድ አብዱላሂ መሃመድ ዛሬ ማለዳ ላይ ነበር ለይፋዊ የሥራ ጉብኝት አዲስ አበባ የገቡት።

ጉብኝታቸውም በአፍሪካ ቀንድ ሠላምና ደኅንነት ለማስጠበቅ ምጣኔ ሃብታዊ ውህደት ለማምጣት እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት የበለጠ በሚጠናከሩበት ጉዳዮች ላይ ትኩረት የሰጠ መሆኑንም ከጠቅላይ ሚኒስትር ፅህፈት ቤት የተገኘው መረጃ ያመለክታል።

ሁለቱ መሪዎች ባደረጉት የሁለትዮሽ ውይይትም የአገሮቹ ግንኙነት ሊጠናከሩ በሚችሉባቸው ምቹ ሁኔታዎች ላይ መክረዋል።

ጎን ለጎንም በአፍሪካ ቀንድ አገሮች ሰላምና ደኅንነት ለማረጋገጥ የሚከናወኑ ተግባራት የበለጠ ለማጠናከር ተስማምተዋል።

ሁለቱ መሪዎች፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮቹና የሶማሊያ ቀዳማዊ እመቤትን ችግኞች ተክለዋል።

 ፕሬዚዳንቱ ዛሬ ማለዳ አዲስ አበባ ቦሌ አለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ሲደርሱ ጠቅላይ ሚንስትር ዶክተር አብይ አህመድ፣ የውጭ ጉዳይ ሚንስትሩ    አቶ ገዱ አንዳርጋቸውና ሌሎች ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች አቀባበል አድርገውላቸዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም