በምርጥ ዘር እጥረት ምክንያት ዘር መዝራት አልቻልንም ...የምዕራብ ወለጋ ዞን አርሶአደሮች

ግንቦት 20/2011 በምርጥ ዘር እጥረት ምክንያት ለመኽር እርሻ ዘር መዝራት አልቻልንም ሲሉ አስተያየታቸውን የሰጡ የምዕራብ ወለጋ ዞን አርሶ አደሮች ተናገሩ ፡፡
ከዞኑ አርሶ አደሮች መካከል በመነ ሲቡ ወረዳ የመጣሪ ብርቢርሳ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር አምባዬ ገለታ እንዳሉት ሁለት ሄክታር መሬት በጊዜ አርሰውና አለስልሰው ለዘር ቢያዘጋጁም ምርጥ ዘር ማግኘት አልቻሉም።

ምርጥ ዘር ለማግኘት ወደ ወረዳው የእርሻና ተፈጥሮ ሀብት ጽህፈት ቤት በየጊዜው ቢመላለሱም አስካሁን ባለማግኘታቸው መሬታቸውን መዝራት እንዳልቻሉ ተናግረዋል፡፡

የኦምቦሻ ኢየሱስ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ስማቸው ለገሠ በበኩላቸው የአፈር ማዳበሪያ በጥሩ ሁኔታ እየቀረበ ቢሆንም የበቆሎ ምርጥ ዘር ባለመኖሩ ያዘጋጁትን አንድ ሄክታር መሬት እስካሁን ሳይዘሩ መቀመጣቸውን ገልጸዋል፡፡

 ምርጥ ዘር ፍለጋ በየጊዜው የአምስት ሰዓት መንገድ በእግራቸው ተጉዘው ወደ ወረዳው የእርሻና የተፈጥሮ ሀብት ጽህፈት ቤት ቢመላለሱም አለማግኘታቸውን የተናገሩት ደግሞ የጨፍጨፊ ባቦ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ቤካማ ከድር ናቸው ፡፡

የወረዳው የገበሬዎች የሕብረት ሥራ ማህበራት ማደራጃና ማስፋፊያ ኤጀንሲ የግብዓት አቅርቦትና ስርጪት የሥራ ሂደት አስተባባሪ አቶ ኤቢሣ ታምሩ የምርጥ ዘር እጥረት መኖሩን አምነዋል።

በወረዳው ለሚገኙ 3ሺህ ለሚጠጉ አርሶ አደሮች የቀረበው ምርጥ ዘር 418 ኩንታል ብቻ መሆኑን ገልጸው፣ ፍላጎትና አቅርቦት በየዓመቱ እየጨመረ በመምጣቱ ለማመጣጠን እንዳልተቻለ ገልጸዋል።

ዘንድሮም ከፍተኛ የሆነ ምርጥ ዘር እጥረት መከሰቱን ነው የተናገሩት።

የዞኑ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ጽህፈት ቤት የምርት ማሳደጊያ አቅርቦትና ሥርጭት የሥራ ሂደት አስተባባሪ አቶ አበበ ፀጋዬ በበኩላቸው ለ2011/2012 የምርት ዘመን በዞኑ ለሚገኙ 20 ወረዳዎች 8 ሺህ 914 ኩንታል ምርጥ የበቆሎ ዘር ለማቅረብ ታቅዶ የተገኘው 5 ሺህ 740 ኩንታል ብቻ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡

በዘንድሮው ዓመት የቀረበው ምርጥ ዘር ካለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጻር በ20 በመቶ ቅናሽ ማሳየቱን የገለጹት አቶ አበበ፣ የተገኘው ምርጥ ዘር 22ሺህ 960 ሄክታር መሬት ማልማት እንደሚችልና 46 ሺህ የሚጠጉ አርሶ አደሮችን ብቻ ተጠቃሚ እንደሚያደርግ ተናግረዋል፡፡

በዞኑ በብዛት የበቆሎ ምርጥ ዘር የሚጠቀሙ የቤጊ፣ የቆንደላ፣ የባቦ ጋምቤል እና የመነ ሲቡ ወረዳዎች ምረጥ ዘሩን ባለማግኘታቸው ችግር ውስጥ መውደቃቸውን ገልጸው፣ ታርሶ የተዘጋጀው መሬት ሳይዘራበት እንዳይቀር አርሶ አደሮች የአካባቢውን በቆሎ መጠቀም እንዳለባቸው አስረድተዋል፡፡

ያጋጠመው የምርጥ ዘር እጥረት  ምርትና ምርታማነትን ለመጨመር ሙሉ የግብር ፓኬጅ በሚጠቀሙና በኩታ ገጠም የሚያለሙ አርሶ አደሮች ላይ አሉታዊ ተጽህኖ እንደሚያሳድርም አቶ አበበ አመልክተዋል።

በተመሳሳይ ዜና በምስራቅ ወለጋ ዞን ለ2011/2012 የምርት ዘመን የምርጥ ዘር አቅርቦት 18 በመቶ መቀነሱን የዞኑ የእርሻና የተፈጥሮ ሀብት ጽህፈት ቤት አስታውቋል ፡፡

የጽህፈት ቤቱ  የግብዓት አቅርቦትና ሥርጭት የሥራ ሂደት ቡድን መሪና የጽፈት ቤቱ ተወካይ አቶ አስፋው ሐምቢሣ እንዳሉት 37ሺህ 335 ኩንታል የተለያዩ የበቆሎ ምርጥ ዘር ለአርሶ አደሩ ለማቅረብ ቢታቀድም ማቅረብ የተቻለው 27 ሺህ 826 ኩንታል ብቻ ነው።

ይህም ካለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር በ18 በመቶ ቅናሽ እንዳለው ነው የገለጹት።

ክፍተቱን ለመሙላት ከሌሎች ዞኖችና ክልሎች ተጨማሪ ምርጥ ዘር ለማግኘት የማፈላለግ ሥራ እየተሰራ መሆኑን ጠቁመው፣ ምንም አማራጭ ከሌለ የምረት ቅናሽ ቢኖረውም በአካባቢውን ዘር ለመጠቀም እንደሚገደዱ ተናግረዋል፡፡

የክረምት እርሻ ዝግጅትን በተመለከተ በምሥራቅ ወለጋ ዞን በምርት ዘመኑ ለማረስ ከታቀደው 407 ሺህ 692 ሄክታር መሬት ውስጥ እስካሁን ድረስ 265 ሺህ ሄክታር መሬት ታርሷል።

ከእዚህ ውስጥ 54ሺህ 471 ሄክታር መሬት በበቆሎና በማሽላ ዘር መሸፈኑም ታውቋል ፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም