ፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ በደቡብ አፍሪካ ፕሬዚዳንት በዓለ ሲመት ላይ ለመታደም ወደ አገሪቱ አመሩ

74

ግንቦት 16/2011 ፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ በደቡብ አፍሪካ ፕሬዚዳንት ሲሪል ራማፖሳ በዓለ ሲመት ላይ ለመታደም ወደ አገሪቱ አቀኑ።

ደቡብ አፍሪካ የፕሬዝደንት ሲሪል ራማፎዛን በዓለ ሲመት ነገ የምታከብር ሲሆን በዚሁ ስነ ስርዓት ላይ ለመሳተፍ ፕሬዝደንት ሣህለወርቅ ዘውዴ ዛሬ ከቀትር በኋላ ወደ ደቡብ አፍሪካ መጓዛቸውን ከፕሬዚዳንት ጽህፈት ቤት የተገኘው መረጃ ያመለክታል።

የበዓለ ሲመቱ ስነ ስርዓት በፕሪቶሪያ በሚገኘው ሎፍቱስ ቨርስፊልድ ስታዲየም የሚከናወን ሲሆን የተለያዩ አገራት መሪዎች ፤የዓለም አቀፍ ድርጅት ተወካዮች እንዲሁም በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ደቡብ አፍሪካውያን እንደሚሳተፉ ይጠበቃል።

ከሁለት ሳምንት በፊት በደቡብ አፍሪካ በተካሄደው አጠቃላይ ምርጫ ገዢው ፓርቲ  የአፍሪካ ብሄራዊ ኮንግረስ ማሸነፉን ተከትሎ የአገሪቱ ፓርላማ ሲሪል ራማፖሳን ከትናንት በስቲያ በፕሬዚዳንትነት መሰየሙ የሚታወስ ነው።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም