የብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ከ9 ቢሊዮን ብር በላይ ማባከኑ ተገለጸ

142
አዲስ አበባ ግንቦት 29/2010 የብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ከ9 ቢሊዮን ብር በላይ ማባከኑን የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አስታወቀ። የምክር ቤቱ የመንግስት ልማት ድርጅቶች ጉዳዩች ቋሚ ኮሚቴ የኮርፖሬሽኑን ያለፉት ዘጠኝ ወራት እቅድ አፈፃፀም ገምግሟል። ተቋሙ የገበያ ጥናት ሳያደርግ ከ9 ቢሊዮን ብር በላይ የሚገመቱ የተለያዩ ማሽኖች መለዋወጫ እቃዎችና መሳሪያዎችን በማምረት አከማችቶ እንዲቀመጡ ማድረጉን የቋሚ ኮሚቴ አባላቱ ተናግረዋል። ድርጅቱ የአገሪቱን ኢኮኖሚ ሊደግፍ በሚችል መልኩና በጥናት ላይ ተመስርቶ እየሰራ አለመሆኑን አባላቱ በግምገማው ላይ አንስተዋል። የቋሚ ኮሚቶው ሰብሳቢ አቶ ገብረእግዝአብሔር አርአያ እንደገሉጸት ኮርፖሬሽኑ የተጀመሩ ፕሮጀክቶን ለማጠናቀቅ ረጅም ጊዜ እየወሰደበት ነው ብለዋል። ተቋሙ በየጊዜው ለምክር ቤቱ የሚያቀርባቸው ሪፖርቶች ወጥነት የጎደላቸውና የሚዋዥቁ ናቸው ያሉት አቶ ገብረእግዚያብሄር ለአብነትም የያዩ ማዳበሪያ ፕሮጀክት አፈጻጸም ሪፖርት ተአማኒነቱን ጥያቄ ውስጥ የከተተው ነው ብለዋል። በተጨማሪም የኦሞ ከራዝ ቁጥር 1 እና የበለስ ቁጥር 1 ስኳር ፋብሪካዎች ግንባታቸው ከ90 በመቶ በላይ እንደተጠናቀቁ ከአንድ ዓመት በፊት የተገለጸ ቢሆንም በ2010 ዓ.ም የእቅድ አፈጻጸም ሪፖርት ግን ከአምናው ያነሰ ሆኖ ሪፖርት መቅረቡን ጠቅሰዋል። በዚህም ምክንያት ለስኳር ፕሮጀክቶቹ በሚል የተተከሉ የሸንኮራ አገዳ  ምርቶች በመድረሳቸው ከፍተኛ ብክነት መድረሱን አንስተው ገበያ ተኮር የሆኑ ምርቶችን እያመረተ እንዳልሆነም ተገልጿል። የአገሪቱን ኢኮኖሚ ሊደግፍ በሚችል መልኩና በጥናት ላይ ተመስርቶ ባለመስራቱ 4 ነጥ4 ቢሊዮን ብር ዋጋ ያላቸው የእርሻ መሳሪያዎችና የመለዋወጫ እቃዎች በአዳማ የእርሻ መሳሪያዎች ኢንዱስትሪ ክምችት ውስጥ እንዲቀመጥ ማድረጉን ጠቁመዋል። በቢሾፍቱ አውቶሞቲቭ ኢንዱስትሪ ክምችት ክፍል ዶግሞ  4 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር የሚያወጡ የተለያዩ መለዋወጫዎች ያለስራ በመቀመጣቸው ለብክነት እየተዳረጉ መሆኑ ተጠቅሷል። ኮርፖሬሽኑ ታላቁ የኢትዮዽያ ህዳሴ ግድብንና ሌሎች ሜጋ ፕሮጀክቶችን እንዲገነቡ በማድረግና የብዙሃን ትራንስፖርት አገልግሎት ሰጭ አውቶብሶችን በመገጣጠም ከፍተኛ አስተዋጾ እያደረገ ቢሆንም ስራዎቹን በወቅቱ በማጠናቀቅ በኩል ችግሮች አሉበትም ብለዋል። ኮርፖሬሽኑ ባለው የመልካም አስተዳደር ችግሮችና አነስተኛ ክፍያ ምክንያት ለተከሰተው የሰራተኛ ፍልሰት መፍትሔ እንዲሰጠውም በቋሚ ኮሚቴው ተጠይቋል። አዲሱ የተቋሙ አመራር ኮርፖሬሽኑ የአገሪቱን ኢኮኖሚ ሊደግፍ በሚችል መልኩና በጥናት ላይ ተመስርቶ እንዲሰራ የማስተካከያ እርምጃ እንዲወስድም ቋሚ ኮሚቴው ጠይቋል። በቅርቡ የኮርፖሬሽኑ ዋና ዳይሬዶክተር ሆነው የተሾሙት ዶክተር  በቀለ ቡላዶ በበኩላቸው በተቋሙ ውስጥ የመንግስትን የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅዱን የሚደግፍ ትልቅ አቅም መኖሩን ተገንዝበናል ብለዋል። ፕሮጀክቶች በተያዘላቸው ጊዜ እየተከናወኑ አይደለም፤  የውጤታማነትና የሀብት ብክነት ችግሮች መኖራቸውን አረጋግጠናል ፤ በቀጣይ ችግሮቹን ለማስተካከል ይሰራል ብለዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም