የኦሮሚያ ክልል ልኡካን ቡድን ጋምቤላ ከተማ ገባ

112

ግንቦት 11/2011 በኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ሽመልስ  አብዲሳ የሚመራ ልኡካን ቡድን  ነገ በሚካሄደው የጋምቤላና ኦሮሚያ ክልሎች  ህዝባዊ  መድረክ ላይ ለመሳተፍ ዛሬ ምሽት ጋምቤላ  ከተማ  ገቡ።

ልኡካን ቡድኑ ጋምቤላ ሲገቡ በክልሉ ከፍተኛ አመራሮችና በከተማው ነዋሪዎች ደማቅ አቀባበል ተደርጎላቸዋል።

የነገውን መድረክ አስመልክቶ የጋምቤላ ክልል የፕሬስ ሴክሬታሪያት ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶኡዶል አገዋ  እንደተናገሩት የጋምቤላና የኦሮሚያ ክልሎች ህዝቦች የረጅም ጊዜ ማህበራዊና  ኢኮኖሚያዊ  ግንኙነት  ያላቸው ናቸው።  

ህዝባዊ መድረኩ በሁለቱ ክልሎች ህዝቦች መካከል ያለውን የቆየ የወንድማማችነትና የአብሮነት እሴት  ይበልጥ  በማጠናከር በጋራ አብሮ የመልማት ታሪካቸውን ለማጎልበት ያለመ መሆኑን ገልጸዋል።

የኦሮሚያ ክልል የመንግስት ኮሙዩኒኬሽን ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ደሬሳ ተረፈ በበኩላቸው የጋምቤላና  የኦሮሚያ ክልል ህዝቦች ለዘመናት መልካም ግንኙነትና ጉርብትና ያላቸው መሆናቸውን ተናግረዋል።

ህዝባዊ መድረኩን ማካሄድ ያስፈለገውም የህዝቦችን የቆየ አብሮነትና  ወንድማማችነት  ይበልጥ በማጠናከር የጋር ማህበራዊና ኢከኖሚያዊ ተጠቀሚነታቸውን ለማረጋገጥ  በማለም እንደሆነ ተናግረዋል።

የክልሉ ከፍተኛ አመራርና የጋምቤላ ከተማ ነዋሪዎች በህዝባዊ መድረኩ  ለመሳታፍ  ወደ ክልሉ ሲገቡ ለተደረገላቸው ደማቅ አቀባበል ምስጋናችውን አቅርበዋል።

በነገው እለት በሚካሄደው ህዝባዊ መድረክ የሁለቱን ህዝቦች የቆየ ማህበራዊና ኢኮኖሚዊ ግንኙነት የተመከተ  ጥናዊ ጽሁፍ ይቀርባል ተብሏል።

ለአንድ ቀን በሚካሄደውበዚሁ መድረክ ከሁለቱ ክልሎች የተውጣጡ ከአንድ  ሺህ የሚበልጡ  ከፍተኛ አመራሮች ፣የሀገር ሽማግሌዎች፣ አባገዳዎችና የተጎራባች  ወረዳ ነዋሪዎች ተሳታፊ እንደሚሆኑ ታውቋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም