በፌደራሊዝምንና ዘላቂ ሰላም ላይ ትኩረቱን ያደረገ ዉይይት ተካሄደ

91

ግንቦት 10/2011 የጠቅላይ ሚንስትር ጽህፈት ቤት "ስለ ኢትዮጵያ እንነጋገር" በሚል ሃሳብ ለ5ኛ ጊዜ ያዘጋጀው ውይይት ፌደራሊዝምንና ዘላቂ ሰላም ላይ ትኩረቱን አድርጎ ተካሄዷል።

የውይይቱ ዋነኛ ዓላማ ሃሳብን ከጎዳና ወደ መድረክ በማምጣት ለሁሉም የምትበቃ ኢትዮጵያን መገንባት ሲሆን፤ በዛሬው መድረክ የፖለቲካ ፓርቲ መሪዎች ምሁራንና የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ተሳትፈዋል።

ጠቅላይ ሚነስትር ዶክተር አብይ አህመድም ከታዳሚዎች መካካለ አንዱ ናቸው።

"ፌደራሊዝም፣ ሰላምና የህዝብ ተሳትፎ" ላይ የሚያተኩሩ የውይይት መነሻ ጽሁፎች በዶክተር ሰሚር አሚን፣ ፕሮፌሰር  እዝቂያስ አሰፋ፣  ዶክተር ኤልሳቤጥ ወልደ  ጊዮርጊስና አቶ አንዷለም አራጌ ቀርበው የተለያዩ ሃሳቦች ተንሸራሽረዋል።

በአዲስ አበባ ዮኒቨርሲቲ መምህር ዶክተር ሰሚር አሚን የኢትዮጵያ  ፌደራሊዝም  የብሄር ጥያቄንና ጎምቱ የሆነውን የተማከለ አስተዳደር በአንድ ላይ አጣምሮ ሊተገብር መሞከሩ ትልቅ ፖለቲካዊ ተቃርኖ ፈጥሯል ብለዋል።

የፌደራሊዝም ስርዓቱ በአንድ በኩል እራስን በራስ የማስተዳደር መብትን ይፈቅዳል፤ በሌለ መልኩ ከማዕከል ሆነኖ ሁሉን ነገር ለመቆጣጠር እንደሚፈልግ አብራርተዋል።

ይህ የተቃርኖ ችግርም "የግለስብና የቡድን መብቶች እንዲሁም አብሮነት" የሚሉ ጽንሰ ሃሳቦች ማስታረቅ የሚቻልበትን ግልጽ መፍትሄ ማበጀት ላይ ማነቆ መሆኑን ተናግረዋል።

በመሆኑም "ፌደራሊዝም ይጠቅማል አይጠቀም' ከሚለው ክርክር ወጥተን ፌደራሊዝሙ እንዴት እነዚህን ሀሳቦች ያስታረቅ የሚለው ላይ ማተኮር ይገባል" ብለዋል።

የፌዴራል ስርዓቱ የግለሰብና የቡድን መብቶችን እንዲሁም  አብሮነትን  አጣምሮና  የዴሞከራሲ  መርሆዎችን ጠብቆ ሊተገበር ይገባል ሲሉም አብራርተዋል።  

ፖለቲከኛውአቶ አንዷለም አራጌ በበኩላቸው ኢትዮጵያ በለውጥ ጎዳና ውስጥ መሆኗ የማይካድ ሃቅ ነው ሲሉ አጽኖት ሰጥተው ተናግረዋል።

"አገሪቱ አሁን ላይ ሊወለድ ባለ የአቃፊ ለውጥ ምጥና ሊሞት ባለ አፋኝ ስርዓት ግብግብ መካካል ትገኛለች" ሲሉ ነው ሂደቱን የገለፁት አቶ አንዷለም።

በለውጥ ሂደት ውስጥ ባለ አገር የተለያዩ ግጭቶች ማጋጠማቸው የሚጠበቅ መሆኑን ጠቁመው፤ ሆኖም መንግስት በሆደ ሰፊነትና በህግ ማስከበር መካካል ግልጽ ደረቅ መሬት ሊያስቀምጥ ይገባል ብለዋል።

በሌላ መልኩ ሰላምን በሚያደፈርሱ አከላት ላይ እርምጃ በመውሰድ ብቻ ዘላቂ ሰላምን ማስፈን አይቻልም ያሉት ደግሞ የግጭት አፈታት ምሁሩ ፕሮፌሰር ህዝቄያስ አሰፋ ናቸው።

እንደርሳቸው እምነት ዘላቂ ሰላም የሚመጣው  ህግ ከማስከበር  ባለፈ  መሰረታዊ  የዜጎቸን  ጥያቄ በመፍታት ነው።

ይህ እውን የሚሆነው ደግሞ በዜጎች መካከል ውይይትና መደማማጥን መፍጠር ከተቻለ ብቻ መሆኑን ጠቅሰው፤ እያንዳንዱ ዜጋ እርሱ የሚሻውን ጥቅም ሌሎች እንደሚፈልጉት ሊገነዘብ እንደሚገባም መክረዋል።

የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ መምህር ዶክተር  ኤልሳቤጥ  ወልደ  ጊዮርጊስ  በበኩላቸው  በኢትዮጵያ እየታዩ ያሉ ችግሮችን ለመፍታትም ሆነ የታቀዱ ህለሞችን ለማሳካት በመጀመሪያ ደረጃ አሳታፊ ስርዓት ሊፈጠር እንደሚገባ ይናገራሉ።

ለዚህ ደግሞ የተዛባው የአገሪቱ ታሪካዊ ትርክት መስተካከል እንዳለበት ነው የገለጹት።

የሲቪክ ማህበራትም ቢሆኑ ኢትዮጵያውያን ባሉበት ነባራዊ  ስነ-ልቦና  የታነጹ  ሳይሆን፤ ስራዎቻቸውን በረጂ ድርጅቶችና አገራት የአእምሮ ትርክት መሰረት የሚከውኑ መሆናቸውንም አውስተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም