የአፋን ኦሮሞ ጥናትና ምርምር ጉባኤ በመቱ ዩኒቨርስቲ

222

ምናሴ ያደሳ(መቱ ኢዜአ )

የመቱ ዩኒቨርስቲ ሰሞኑን የአፋን ኦሮሞ ምርምር ጉባኤ አካሄዷል። ዩኒቨርስቲው በአፋን ኦሮሞ ምርምር ላይ ያተኮረ ጉባኤ ሲያዘጋጅ ይኽው የመጀመሪያው ነው።

በጉባኤው ላይ በሀገሪቱ የተለያዩ ዩኒቨርስቲዎች የሚያስተምሩ የቋንቋው ምሁራን ተካፍለዋል። ከ15 በላይ በአፋን ኦሮሞ ላየ አተኩረወ የተካሄዱ የምርምር ስራዎች ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል።

ከቀረቡት የምርምር ስራዎች መካከል የአፋን ኦሮሞ ስነቃል(Afoola Afaan Oromoo) ላይ ያተኮሩ፣ የኦሮሞ ባህል፣ ቋንቋ ታሪክና ማንነት ለማጎልበት እየተከናወኑ  ያሉ ተግባራት እና የሚስተዋሉ ችግሮች ተዳስሰዋል ።

 ከሀገራዊ ለውጡ ወዲህ  የኦሮሞ ህዝብ ጥያቄ በትክክለኛው መንገድ በማሳየት ረገድ ሚድያዎች የተጫወቱት ሚናና በአሰራር ረገድ የታዩ  ተግዳሮቶችም ከቀረቡት የምርምር ስራዎቸ መካከል ተጠቃሾች ናቸው ።

የኦሮሞ ስነቃል (Afoola) የኦሮሞ ህዝብ ታሪክ ፣አኗኗርና ማንነት የሚንጸባረቅበት ጥበብ ቢሆንም በማስተዋወቅና በስነጽሁፍ አደራጅቶ በማስቀመጥ ረገድ ውስንነቶች እንዳሉ በጥናቱ ተጠቁሟል ።

የጅማ ዩኒቨርሲቲ መምህር ዶክተር ደረጀ ፉፋ ባቀረቡት ጥናታዊ ጽሁፍ የኦሮሞ ህዝብ ታሪክ፣ ባህልና ማንነት በአብዛኛው በኦሮሞ ስነቃል(Afoola) ውስጥ ይገኛሉ። የኦሮሞን ስነቃል(Afoola) የማያውቅ ሰው ስለ ኦሮሞ ህዝብ ታሪክ እና ማንነት መረዳት እንደሚያስቸግረው ነው የተናገሩት።

ለዚህ ደግሞ እንደምክንያት የሚያስቀምጡት ቋንቋው ለረዥም ዘመናት በደረሰበት ጫና በስነቃል ( Afoola) ያሉትን በስነጽሁፍ ማዘጋጀት ባለመቻሉ ነው።

የኦሮሞ ስነቃል( Afoola Afaan Oromoo) የኦሮሞ ህዝብ በሰርግ፣ በተለያዩ ሃይማኖታዊ ስነ ስርአቶች፣በህብረት ስራ እና በመሳሰሉት መልዕክቶችን በቀላሉና ሳቢ በሆነ መንገድ የሚያስተላለፍበት ነው።

የኦሮሞ ህዝብ ባህል፣አኗኗር፣ታሪክ ወግና ልማድ ከትውልድ ወደ ትውልድ ሲያስተላልፍ የቆየው በስነቃል( Afoola)መሆኑን ዶክተር ደረጀ ባቀረቡት ጽሁፋቸው አመልክተዋል።

ሰነቃል( Afoola) ከኦሮሞ ህዝብ ጋር እጅግ የተቆራኘ ነው። የተጣላ ሲታረቅ ፣ በሙግት ፣በጦርነት፣ በአደንና በደስታ ወቅቶች በስፋት ጥቅም ላይ ይውላል።

ባህላዊ የቤት አሰራር፣ የምርት አመራረት፣ ማህበራዊ መስተጋብሮች፣ የአለባበስና አኗኗር ፣ሞትና ውልደትበመሳሰሉትም ጥቅም ላይ የሚውል ነው።

የኦሮሞ ስነቃል( Afoola Afaan Oromoo) የሚባሉት Mammaaksa( መማክሳ)፣ Hibboo Hibbaka(ሂቦ ሂበካ) ፣ Oduu duri(ኦዱ ዱሪ) ፣Jechama (ጄቸማ) ፣Soorgoof Sookkoo( ሶርጎና ሶኮ) እና Baacoo(ባጮ) ናቸው።

Mammaaksa( መማክሳ) ማለት በደቦ ስራ፣ በተለያዩ ማህበራዊ ግንኙነቶች፣ በደስታ ፣ በሀዘን፣በጦርነት፣በብሶትና መሰል ወቅቶች በቁጥብ ቃላትና አነስተኛ ስንኞች ሳቢ በሆነ አገላለጽ ጥቅም ላይ የሚውልነው፡

በስፋት ከሚታወቁ የMammaaksa (መማከሳ) አይነቶች ጥቂቶቹን ለመግለጽ ያህል Saree Gowwaan dhadhaa kajeelti.( ሞኝ ውሻ ቅቤ ይከጅላል) ፣Karaaf Garaan addaan nama baasa( ሆድና መንገድ ሰው ያለያያል) ፣Osoon gubadhuun kolfa jette akaayiin( እየተቃጠልኩ እስቃለሁ አለች ቆሎ) የሚሉ ይገኙበታል ።

 Geerarsa(ጌረርሳ) የተባለውና ታዋቂ የሆነው የኦሮሞ የዘፈን ስልት ሙሉ ለሙሉ ማለት በሚቻል መልኩ በዚሁ ስነቃል( Afoola) የሚዋቀር ነው።

ሌላኛው የኦሮሞ ስነቃል (Afoola) Jechama (ጄቸማ) ነው። ይህ ስነቃል ሳቢ እና አጭር ዓረፍተ ነገርን በምሳሌ እያዋዙ መልዕክት የሚያስተላልፉበት ነው።

 Gara laafessa( ገራ ላፌሳ) እና  Ulee biyyaa (ኡሌ ቢያ) የሚባሉት ደግሞ ከኦሮሞ Jechama (ጄቸማ) ጥቂቶቹ ናቸው።

 ለምሳሌ ከደቦ ስራ በኋላ ለመስተንግዶ ቤት ውስጥ የተሰባሰቡ ሰዎች በምግብና መጠጥ ላይ እያሉ በድንገት የመጠጥ አቅርቦት ካነሰ አንዱ ይነሳና እንዲህ ይላል።

Harkisaa Farda Collee( ያቺን ጮሌ ፈረስ ሳብ አርጉልን)

Gadifidaa daadhii sanaa( ጠጅ አንሷል ወጣ አድርጉልን)

Yoo dhume waasiin anaኣ ( ካለቀ ዋስ እኔው ነኝ)

ታዳሚውም ተቀብሎ በዜማ መልክ ካንጎራጎረ በኋላ የቤቱ አስተናጋጆች ጠጁን ለተሰብሳቢዎቹ ያቀርባሉ።

የኦሮሞ ስነቃል( Afoola) ጥልቅ የሆነና በጥበብ የተሞላ ቢሆንም ከቃል ባለፈ በስነጽሁፍ መልኩ በስፋትባለመዘጋጀቱ የህዝቡ ወግ፣ባህል፣ታሪክና ማንነት በስፋት እንዳይታወቅ አድርጓል ይላሉ ዶክተር ደረጀ።

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የኦሮሞ ቋንቋ ምሁራን በስነጽሁፍ መልክ በማዘጋጀት ለማስተማሪያ እንዲውል በማድረግ ላይ ቢሆኑም እስካሁን የተሰሩት ስራዎች ከሀብቱ ስፋት አንጻር ጥቂት ብቻ ናቸው ። ለዚህም ሁሉም እንዲረባረብ ነው መልዕክታቸውን ያስተላለፉት።

ሌላኛው በመድረኩ ላይ ጥናታዊ ጽሁፋቸውን ያቀረቡት የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግረስ ምክትል ሊቀመንበር አቶበቀለ ገርባ ናቸው።

አቶ በቀለ በፅሁፋቸው  አንድ ቋንቋ ጎልብቶ ወደ ቀጣዩ ትውልድ እንዲተላለፍ በትምህርት ተቋማት፣በመገናኛ ብዙሀንና በስራ ቦታ በአግባቡ በስራ ላይ መዋል አለበት።

አንድ ቋንቋ በአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ለመማሪያነት ሲያገለግልና አለፍ ብሎ በሁለተኛ ደረጃና በከፍተኛትምህርት ተቋማት ለመማርያነት ሲውል ጥንካሬው እንደሚለያይ ገልጸው፣  ቋንቋው እያደገ እንዲሄድ እስከ ምርምር ደረጃ ሊያገለግል ይገባል ነው ያሉት።

ተማሪዎችም በቋንቋቸውን ብቻ መማር ሳይሆን ቴክኖሎጂ፣ጤና፣ህግና ለመሳሰሉትን ዕውቀቶች መቅሰሚያ አድርገው ሲጠቀሙበት የበለጠ እያደገ እንደሚሄድ አስረድተዋል ።

በስራ ቦታም ቋንቋው በአግባቡ ጥቅም ላይ ሊውል ይገባል። የመገናኛ ብዙሃንም በተለያዩ ቋንቋዎች ሳቢ እና ማራኪ ፕሮግራሞችን በማስተላለፍ የቋንቋውን ተጠቃሚዎች አድማጭነት ካላረጋገጡ ለቋንቋው ዕድገት የሚኖራቸው ሚና አነስተኛ ሊሆን እንደሚችል ነው ያብራሩት።

የወሎ ዩኒቨርስቲ የፖለቲካል ሳይንስ መምህር አቶ ሽመልስ ሀብታሙ በበኩላቸው የመገናኛ ብዙሀን፣ የሽግግር ፖለቲካውና የኦሮሞ ህዝብ ጥያቄ በሚል ባቀረቡት ጽሁፍ የመገናኛ ብዙሀን ከ ኢ-ዲሞከራሲያዊ ወደ ዲሞክራሲያዊ መንግስት በሚደረገው ለውጥና ሽግግር  የህዝቡን ጥያቄዎች በማሳየት ለዲሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታ የቀዳሚነት ሚና ሊጫወቱ ይገባል ነበር ያሉት ።

በአደጉት ሃገራት ጀርባ ጠንካራ ሚዲያ ለቀውስ ከተዳረጉት ሀገራት ጀርባ ደግሞ ሃላፊነት የጎደላቸው ሚዲያዎች እንዳሉ ገልጸው ለዚህም የሩዋንዳን ግጭት አንስተዋል።

ከዚህ አንጻር ከለውጡ ወዲህ በሃገራችን የሚገኙ አንዳንድ የመገናኛ ብዙሀን የህዝቡን ጥያቄዎች ፍትሃዊናትክክለኛ በሆነ መልኩ በመግለጽ ረገድ ችግር እንዳለባቸው አመልክተዋል።

በተለይ ካለፉት ሶስት ወራት ወዲህ በማህበራዊ ሚዲያዎችና  በአንዳንድ የመገናኛ ዘዴዎች ህዝቦችን በመለያየት የኦሮሞን ህዝብ ጥያቄና አቋም ሆን ብለው አዛብተው በማቅረብ ሃላፊነት የጎደለው ስራ ሲሰሩ እንደሚስተዋሉ ተናግረዋል።

 ``ቋንቋ እና ሀገራዊ መንግስት ግንባታ`` በሚል የጥናት እና ምርምር ስራ ማከናወናቸውን ገልጸው ። በዚህም ከዚህ ቀደም በሀገሪቱ የነበረው የአንድ ቋንቋ ፖሊሲ ሌሎች ቋንቋዎችን ከማቀጨጩም ባለፈ በኢኮኖሚውና ማህበራዊ ትስስር ረገድ ማበርከት የሚገባቸውን ጠቀሜታ ማስቀረቱን ተናግረዋል።

ዜጎች እርስ በእርስ ያላቸውን ግንኙነት ለማጠናከርና የፌዴራል ስርአቱን ለማጎልበት አንዱ የአንዱን ቋንቋ እንዲያውቅና እንዲረዳ መደረግ እንዳለበትም አመልክተዋል።

 የመቱ ዩኒቨርስቲ ፕሬዚደንት ዶክተር ተካልኝ ቀጄላ በበኩላቸው አፋን ኦሮሞ ከክልል አልፎ በሀገር አቀፍ ደረጃ ለሀገር ልማትና አንድነት አስተዋጽኦው እንዲያድግ የቋንቋው ተጠቃሚዎችና ሌሎች ብሄረሰቦች የበኩላቸውን ሊወጡ ይገባል።

የቋንቋው መጎልበት የሀገሪቱን አንድነት ከማጠናከር ባለፈ ከጎረቤት ሀገራት ጋር የሚኖረዉን የፖለቲካና ንግድ ትስስር በማጠናከር ረገድ ትልቅ አስተዋጽዎ እንደሚኖረው ተናግረዋል።

የመቱ ዩኒቨርስቲም ካለፈው አመት አንስቶ የኦሮሞ ምርምር ማዕከል በማቋቋም ሳይንሳዊ የሆነ የጥናትና ምርምር ስራ ለማካሄድ እየሰራ እንደሆነ አስታውቀዋል። ማዕከሉ የኦሮሞ፣ ባህል፣ ቋንቋና ማንነት በጥልቀትና ሳይንሳዊ በሆነ መንገድ በማጥናት በሀገር ውስጥና በውጭ በስፋት ለማስተዋወቅ መሆኑን ገልጸዋል። በጥናት የተገኙ ውጤቶችን ለሀገር ግንባታና ዕድገት ለማዋል እንደሚሰራ ተናግረዋል።

የመቱ የኒቨርስቲ በመማር ማስተማሩ ሒደትም ከ2005 ዓም ጀምሮ የአፋን ኦሮሞ ዲፓርትመንት ከፍቶ በመጀመሪያ ድግሪ እያስተማረ ነው።

አፋን ኦሮሞ በአፍሪካ ከስዋህሊ፣ ሀውሳ እና አረብኛ ቋንቋዎች ቀጥሎ ብዙ ተናጋሪዎችን በመያዝ አራተኛ ደረጃ ላይ ቢገኝም እስካሁን የሳይንስና ቴክኖሎጂ፣የምርምርና የኢንተርኔት ቋንቋ ለማድረግ ብዙ ስራዎች ከምሁራን እንደሚጠበቁ ተናግረዋል።

ቋንቋው የኢፌድሪ መንግስት የስራ ቋንቋ ለማድረግ እየተደረጉ ያሉ ጥረቶች ለሀገሪቱ በሁሉም ረገድ ጠቀሜታው የጎላ በመሆኑ ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባው ነው የተናገሩት። ሙሁራንም በዚህ ረገድ የሚጠበቅባቸውን ሚናሊወጡ ይገባል ነው ያሉት።

የመቱ የኒቨርስቲ`` የኦሮሞ ጥናትና ምርምር ስራዎች ለሀገር ግንባታና ልማት ያለው ፋይዳ ``በሚል ያዘጋጀው ጉባኤም የጥናትና ምርምር ስራዎቹ ለሀገር ልማት የሚያበረክቱትን አስተዋጽኦ ለማሳደግ የታቀደ መሆኑንና ለወደፊትም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አብራርተዋል።

በጉባኤው የኦሮሞ ምርምር ማዕከል ወደፊት ሊያተኩርበት ስለሚገባቸው አቅጣጫዎችና የባለድርሻ አካላት ሚና የታየበት መሆኑን ነው የገለጹት።

የሰግለን ኢሉ አባገዳ ከሊፋ ሾኖ እንዳሉት የመቱ ዩኒቨርስቲ ያዘጋጀው የኦሮሞ ጥናትና ምርምር ጉባኤ በቁንቋው ዙሪያ ያሉ መሁራንን በአንድ ቦታ ያገናኘ በመሆኑ ሰፊ የልምድ ልውውጥ የተገኘበት ነው።  

መሰል ስራዎች በሁሉም ደረጃዎች በሚገኙ ተቋማት እንደልምድ ተወስዶ ቋንቋና ባህል በማጎልበት ረገድ ሙሁራን ተቀራርበው እንዲሰሩ ሊደረግ ይገባል ነው ያሉት።

ሙሁራን እና የትምህርት ተቋማት የህዝቡን ባህል ቋንቋና ማንነት ለማሳደግ በሚያደርጉት ጥረት የሚዲያ ተቋማትም እንደ ዋነኛ ባለድርሻ ሆነው በጋራ ሊሰሩ ይገባል።

አፋን ኦሮሞ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ የትምህርት ቋንቋ ከሆነ ጀምሮ እየተከናወኑ ያሉት የጥናትና ምርምር ስራዎች ቋንቋውን በማጎልበትና በማሳደግ ረገድ ትልቅ አስተዋጽኦ ማበርከታቸውን ገልጸዋል። ይህ ጅምር ተጠናክሮ እንዲቀጥል ሙሁራን ይበልጥ ተቀናጅተው ሊሰሩ እንደሚገባ አስገንዝበዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም