የቻይና ባለሀብቶች በኢትዮጵያ በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች እንዲሰማሩ ተጠየቀ

115

አዲስ አበባ ሚያዝያ 17/2011 ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐብይ አህመድ በቻይና ምሥራቃዊ የጠረፍ ግዛት የሚኖሩ ባለሀብቶች በኢትዮጵያ በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች እንዲሰማሩ ጥሪ አቀረቡ።

የዠዢንግ ግዛት ኮሚኒስት ፓርቲ ጸሐፊ ቼ ጁን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድና ልዑካቸው በቻይና ምሥራቃዊ የጠረፍ ግዛትን ለመጎብኘት ወደ ስፍራው ባቀኑበት ወቅት አቀባበል አድርገውላቸዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ባለሀብቶች አዲስ በተከፈቱ የኢንቨስትመንት መስኮች እንዲሳተፉ፣ በተለይም የግብርና ውጤቶችን በማስገባት ላይ በበለጠ እንዲሳተፉ ጥሪ አቅርበዋል።

የግዛቲቱ ባለሀብቶች በኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት እየተንቀሳቀሱ ይገኛሉ።

የዠዢንግ ግዛት በወንዝና ተፋሰሶች ጽዳትና መልሶ ማልማት ሥራ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ሥነ ምሕዳር ክብር አሸናፊ በመሆኗ ሸገርን በማስዋብ ፕሮጀክት ተምሳሌት የምትሆን ናት።

በተያያዘ ዜና ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድና ልዑካቸው ቱባ የኢ-ንግድ ኩባንያ የሆነውን የአሊባባን ዋና መሥሪያ ቤትን በቻይና ሀንግዙ ጎበኝተዋል።

በዚሁ የፈረንጆች  ዓመት መጀመሪያ አካባቢ በስዊዘርላንድ ዳቮስ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የአሊባባ ኩባንያ ሊቀ መንበር የሆኑት ጃክ ማ ጋር መገናኘታቸው ይታወሳል።

የዛሬው ግንኙነታቸውም ባለኃብቱ የኢትዮጵያን ልማትና ዕድገት ለመደገፍ ያለውን  ወዳጅነት አመላካች መሆኑ ተጠቁሟል።

ባለሀብቱ ጃክ ማ ፤ በኢትዮጵያ እየተካሄዱ ባሉት ለውጦች መደነቃቸውንና ኢትዮጵያ ለኩባንያቸው ቁልፍ አጋር በመሆኗም በዚህ ዓመት መጨረሻ ኢትዮጵያን እንደሚጎበኙ ጠቁመዋል።።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም