የካንሰር ህክምና ተደራሽ አለመሆን ህሙማንን ለተጨማሪ እንግልት እየዳረጋቸው ነው

101

 መጋቢት 8/2011 የካንሰር ህክምና ተደራሽ  አለመሆን  ለተጨማሪ  እንግልት  እየተዳረጉ  መሆኑን አስተያየታቸውን  ለኢዜአ  የሰጡ ህሙማን ተናገሩ፡፡

ከአስተያየት  ሰጭዎቹ  መካከል አቶ  ሙህዲን ከድር  የማህጸን ጫፍ ካንርሰር የታመሙባቸውን  ባለቤታቸውን ለማሳከም በርካታ ውጣውረዶችን  ማየታቸውን ይናገራሉ፡፡  

በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል  ህክምናውን ለመጀመር ለአንድ አመት ወረፋ መጠበቅ  እንዳለባቸው  እንደተነገራቸውም ይገልጻሉ።

በሆስፒታሉ በማታው የህክምና ላማሳከምም   ለአራት ወራት መጠበቅ  እንዳለብኝ ተነገረኝ የሚሉት አቶ ሙህዲን፤ የሆስፒታሉ አላማ ህይወትን ማዳን ቢሆንም ቸልተኝነትና በግል ወደ ሚሰጥ አገልግሎት እንደሚገፉት ትዝብታቸውን ተናግረዋል።

 “የሆስፒታል አገልግሎት እንደ መብራት፣ውሃ አግልግሎት ሳይሆን ህይወትን የማዳን ጉዳይ በመሆኑ  ልዩ ትኩረት ሊሠጠው ይገባል” የሚሉት አቶ ሙህዲን በአግልገልግሎት አሰጣጡ ተስፋ  መቁረጣቸውን ተናግረዋል።  

የአስራ ሁለት አመት ታዳጊ  አባይነህ  ቢረሳው በደም ካንሰር ከተያዘ  ሶስት አመታትን አስቆጥሯል፡፡  ህክምናውንም በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል እየተከታተለ  ነው፡፡

ህክምናውን ከጀመረ ወዲህ በአካሉ ላይ የነበረው እብጠት ቢቀንስም  መድሀኒቱ በሚጠፋበት ጊዜ ህክምናው እየተቆራረጥ እየተቸገረ እንደሆነም ይናገራል፡፡

ልጃቸውን ለማሳከም መሬታቸውንና ከብቶቻቸውን  እንደሸጡ የሚናገሩት የአባይነህ ወላጅ አባት አርሶ አደር ቢሪሳው  ተዋበልኝ  ህክምናውን የሚከታተሉት ከጎጃም እየተመላለሱ በመሆኑ  በቤተሰባቸው  ህይወት  ላይ ጫና እንደፈጠረባቸውም ይናገራሉ፡፡

የማቲዎስ ወንዱ የኢትጵያ ካንሰር ሶሳይቲ የህሙማን እንክብካቤ ሃላፊ አቶ ብርሃኑ ሞገስ እንደሚሉት ህሙማኑ የክምና ቀጠሯቸው እስኪደርስ በመጠባበቅ ላይ እያሉ ተራ ሳይደርሳቸው  ለህልፈተ ህይወት ይዳረጋሉ፡፡

በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል የስነ ካንሰር ህክምና ክፍል ሃላፊ ዶክተር አይናለም አብረሃ  እንደሚያብራሩት ከበሽታው መንስኤዎች መካከል የእድሜ መግፋት፣ የአመጋገብ ስርዓት፣ የአኗኗር ዘይቤ፣ ለሱስ ተጋላጭነት፣ የመኖሪያ አካባቢ፣ በቂ እንቅስቃሴ አለማድረግ ይገኙበታል።  

ህክምናው ፣በኬሚካል፣ በጨረር፣ በተናጠል  ወይም በጥምረት ሊሰጥ እንሚችል ያብራሩት ዶክተር አይናለም የቀዶ ህክማናው በማንኛውም ሆስፒታል በቀዶ ህክምና ስፔሻሊስት ሊሰጥ እንደሚችል ተናግረዋል።   

የኬሚካል ህክምና- የኬሞ ቴራፒ በመድሃኒት መልኩ እንደሚሰጥ  የተናገሩት ዶክተሩ  አገልግሎቱ በሃዋሳ ፣በመቀሌና ጎንደር ይሰጣል ብለዋል፡፡

ዶክተር አይናለም  እንደሚሉት የጨረር ህክምና ለማግኘት ህሙማን ረዥም  የጊዜ ቀጠሮ ለመጠበቅ የሚገደዱት ህክምናው  በጥቁር አንበሳ  ሆስፒታል ብቻ ከመሰጠቱም ባለፈ የጨረር ህክምና መስጫው ማሽን አንድ ብቻ በመሆኑ ከታካሚዎች ቁጥርጋር ባለመጣጣሙ ነው፡፡

ችግሩን ለማቃለል የተለያዩ የመፍትሄ እርምጃዎች እየተወሰዱ መሆኑን የሚያብራሩት ዶክተር አይናለም በቅርቡ ማሽኖች ተገዝተው ስራ ለማስጀመር የመገጣጠም ስራ እተከናወነ መሆኑን   ጠቁመዋል።

የህክምናውን ተደራሽነት ለማስፋትም ከአመት በኋላ በሃረማያ፣ በጅማ፣ በጎንደርና በመቀሌ ሊሰጥ እንደሚችል የተናገሩት ዶክተር ዓይናለም  የህክምና ባለሙያ እጥረትን ለማቃለልም ከአምስት ዓመታት በኋላ  ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሰልጥነው የሚወጡ ከ50 እስከ 60 የሚደርሱ የስነ ካንሰር ስፔሻሊስቶች ሊኖሩ እንደሚችሉም ጠቁመዋል፡፡

የማታው ህክና ከበመደበኛው ብዙም የተለየ እንዳልሆነ የተናገሩት ዶክተር ዓይናለም   ህክምናውን ለማግኘት እስከ አራት ወራት ወረፋ መጠበቅ እንደሚያስፈልግ ጠቅሰው ለጊዜው የማታው ህክምና  አገልግሎት  መቋረጡንም  ይናገራሉ፡፡  

በሆስፒታሉ ህክምናውን የሚሰጡ ባለሙሙዎች ቸልተኝነት ይስተዋልባቸዋል የሚል ከህሙማኑ ለተነሳው ቅሬታ  ሲመልሱ፡ “የህክምና ባለሙያዎች ማድረግ የሚችሉትን ከማድረግ ውጪ ከታካሚው ጋር እያለቀሱ ከማባበስ ይልቅ ሙያው በሚፈቅደው ስነ-ምግባር መሰረት ህሙማንን  ማጽናናት እንደሚስፈልግ  ጠቅሰው፣  ሰው ታሞ  ልትረዳው እየቻልክ  በጠቀስኳቸው ችግሮች ሳይታከም ሲቀር የሚሰማንን ስሜት በቦታው ያለ ብቻ ነው የሚውቀው” ይላሉ ፡፡

የህክምናውን ተደራሽነት ለማስፋትም ከአመት በኋላ በሃረማያ፣ በጅማ፣ በጎንደርና በመቀሌ ሊሰጥ እንደሚችል የተናገሩት ዶክተር ዓይናለም  የህክምና ባለሙያ እጥረትን ለማቃለልም ከአምስት ዓመታት በኋላ  ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሰልጥነው የሚወጡ ከ50 እስከ 60 የሚደርሱ የስነ ካንሰር ስፔሻሊስቶች ሊኖሩ እንደሚችሉም ጠቁመዋል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም