''በፌደራል መንግሥት የታቀዱ የባቡር መሥመር ፕሮጀክቶች በፍጥነት ሊጀመሩ ይገባል''-የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር

342

ባህር ዳር መጋቢት 7/2011በአማራ ክልል ይገነባሉ ተብሎ በፌደራል መንግሥት የታቀዱ የባቡር መሥመር ፕሮጀከቶች በፍጥነት እንዲጀመሩ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ዶክተር አምባቸው መኮንን ጠየቁ።

በደቡብ ጎንደር ዞን ወረታ ከተማ የሚገነባውን የደረቅ ወደብና ተርሚናል ግንባታ የመሠረት ድንጋይ ተቀምጧል፡፡

ዶክተር አምባቸው በዚሁ ወቅት እንዳሉት ባቡር ለአገሪቱ የሚያበረክተውን ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ከግምት በማስገባት የተያዘው ዕቅድ ወደ ተግባር መግባት ይኖርበታል።

መሥመሮቹ ከወልዲያ -ወረታ-ፍኖተ ሰላም እንዲሁም ከወረታ- መተማ-ሱዳን ለመዘርጋት የታቀዱ እንደሆኑም አስታውሰዋል፡፡

በዕቅድ ከተያዙት መሥመሮች አንዱም ሥራ ባለመጀመሩ በሕዝቡ ዘንድ ቅሬታ መፍጠሩን ዶክተር አምባቸው ገልጸዋል።

በወረታ ከተማ በ20 ሄክታር መሬት የሚያርፈው የደረቅ ወደብና ተርሚናል ግንባታም አስፈላጊው የመሠረተ ልማት አቅርቦት ካልተሰራለት ውጤታማ ሊሆን እንደማይችል ተናግረዋል፡፡

በክልሉ ከ420 ሺህ በላይ ሕጋዊ ነጋዴዎች እንዳሉ ያስረዱት ርዕሰ መስተዳድሩ፣ ነጋዴዎቹ ተገቢ የመሠረተ ልማት ባለመኖሩ ወደ ክልሉ የሚያስመጡትንም ሆነ ወደ ውጪ የሚልኩትን ምርት በመንገድ መሠረተ ልማት እጥረት አለመሟላት ችግር እንደሚያጋጥመው ተናግረዋል።

ይህምተገቢ ላልሆነ የጊዜና የገንዘብ ወጪ እንደሚዳርጋቸው ዶክተር አምባቸው አስረድተዋል።

ክልሉ ትርፍ አምራችና የአገሪቱን ኢኮኖሚ ለማሳደግ  ከፍተኛ አስተዋጽኦ ስላለው  የፌዴራል መንግሥት ለክልሉ ትኩረት ሊሰጠው ይገባል ብለዋል።

በመንግሥት ላይ ሙሉ ተስፋ ያለው የክልሉ ሕዝብ ይገነባሉ ተብለው ግንባታውን  በጉጉት እየተጠባበቀ ነው ብለዋል።

የትራንስፖርት ሚኒስትሯ  ወይዘሮ ዳግማዊት ሞገስ በበኩላቸው በክልሉ ለመገንባት የታቀዱትን የባቡር መሥመር ዝርጋታ ለማስጀመር ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን  አስታውቀዋል።

ለዚህም የወረታ-ጎንደር-መተማ 504 ኪሎ ሜትር፣በሱዳን በኩል ጋላባት፣ ገዳሪፍ፣ከሰላና ሃያ ሱዳን ወደብ የሚዘረጋ ደረጃውን የጠበቀ የባቡር መሥመር ፕሮጀክት ግንባታ  እውን ለማድረግ ከሱዳን መንግሥት ጋር ስምምነት ላይ ተደርሷል።

ለፕሮጀክቱ መሳካት አስተዋጽኦ የሚያደርግ  የአዋጪነት ጥናት በአፍሪካ ልማት ባንክ አማካኝነት በቅርቡ  እንደሚጀመርም ተናግረዋል።

የወረታ ደረቅ ወደብ ግንባታም ይህንን የባቡር መሥመር  ግንባታ ግምት ውስጥ በማስገባት እንደሚገነባ ገልጸዋል።

የወረታ የደረቅ ወደብና ተርሚናል ግንባታ በ20 ሄክታር መሬት ላይ የሚያርፍ ሲሆን፣ ለመጀመሪያው ምዕራፍ ከ100 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ ይደረጋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም