አድዋን በማስመልከት በሰሜን ሸዋ የተለያዩ አካባቢዎች ጉብኝት እየተካሄደ ነው

74

አዲስ አበባ የካቲት 18/2011 አድዋ የድል በዓልን በማስመልከት ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎችና የመገናኛ ብዙሃን ባለሙያዎች የሰሜን ሸዋ የተለያዩ አካባቢዎችን እየጎበኙ ነው።

123ኛውን ዓመት የአድዋ ድል በዓል በማስመልከት ጉብኝቱን ያዘጋጁት የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር፣ የአማራ ክልል ቢሮ እና የሰሜን ሸዋ ዞን  ባህልና ቱሪዝም  ናቸው።

የሰሜን ሸዋ ዞን አስተዳዳሪ አቶ ተፈራ ወንድምአገኘሁ የአድዋ ድል በዓል ዘንድሮ ለመጀመሪያ ጊዜ በዳግማዊ አፄ ምኒልክ እና ፊትአውራሪ ገበየሁ ካሳ የትውልድ መንደር አንጎለላ መከበሩን ገልጸዋል።

"የአድዋ ድል የአንድነት፣ የሉዓላዊነትና የኩራት ምንጫችን ነው" ያሉት አቶ ተፈራ አድዋን ስንዘክር አጼ ምኒልክን መርሳት የለብንም ብለዋል።

የዳግማዊ አጼ ምኒልክ የትውልድ ቦታ፣ የንጉስ ሳህለስላሴ ቤተ-መንግስት ፍርስራሽና የአንጎለላ ኪዳነ ምህረት ቤተ-ክርስቲያን ሙዚየም ተጎብኝተዋል።

በዚሁ ወቅት የአካባቢው ነዋሪዎች የአማርኛና ኦሮምኛ ባህላዊ ጭፈራዎችንና ባህላዊ የጉግስ ጨዋታን አቅርበዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም