የዛላንበሳ መንገድ የጉምሩክና ሌሎች ስርዓቶች ከተጠናቀቁ በኋላ ዳግም ይከፈታል

66

አዲስ አበባ ታህሳስ 29/2011 ኢትዮጵያና ኤርትራ የሚያገናቸው የዛላንበሳ መስመር የጉምሩክና ሌሎች ስርዓት ከተበጁለት በኋላ ዳግም እንደሚከፈት ተጠቆመ።

ኢትዮጵያና ኤርትራ ሁለት አስርተ ዓመታት የቆየ ቁርሿቸውን ትተው ወደ ሰላም ከተመለሱ ወራቶች ተቆጥረዋል።

ሁለቱ አገራት በመሪ ደረጃ ግንኙነት ከፈጠሩ ከጥቂት ጊዜያት በኋላ መስከረም 1 ቀን 2011 ዓ.ም ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድና የኤርትራው ፕሬዝዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ በተገኙበት የተዘጉ መንገዶች ተከፍተው የህዝብ ለህዝብ ግንኙነቱ በይፋ መጀመሩ ይታወቃል።

ኢትዮጵያን ከኤርትራ ጋር በትግራይ ክልል በኩል የሚያገናኛት የዛልአንበሳ መስመር ደግሞ የአገራቱ መሪዎች በመገኘት  የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት ያስጀመሩበት መንገድ ነው።

የትግራይ ክልል ምክትል ርእሰ መስተዳደር ዶክተር ደብረፂዮን ገብረሚካኤል የሁመራ ኦምነሐጀር መንገድ መከፈትን አስመልክቶ ዛሬ ከጋዜጠኞች ጋር በነበራቸው ቆይታ ሌላኛው ኢትዮጵያና ኤርትራ የሚገናኙበት የዛላአንበሳ መስመር ከሳምንታት በፊት ጀምሮ መዘጋቱን ተናግረዋል።

መንገዱ መዘጋት አስመልክቶ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ ከኤርትራው ፕሬዝዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ ጋር መነጋገራቸውን ጠቁመው፤ መንገዱ የጉምሩክና ተያያዥ ሰርዓቶች ከተበጁለት በኋላ ዳግም እንደሚከፈት ምላሽ መገኘቱን ተናግረዋል።

የድንበር ግንኙነቱ ክፍት የሆነው ለተወሰነ ጊዜ ነው፤ አሁን ግን የጉምሩክ ስርዓት ቁጥጥርም ድንበሩ ላይ የማድረግ  ዝግጅቱን ስለጨረስን ቶሎ ብለን የተዘጋውን መስመር እንከፍተዋለን ብለዋል።

ከዛላንበሳ በተጨማሪ ዛሬ በይፋ የተከፈተውን የሁመራ ኦምነሐጀር መንገድ እንዲሁም ሌሎች የግንኙነት መስመሮች ላይ ስርዓት ለማበጀት መንግስት እየሰራ መሆኑንም ጠቁመዋል።

የሁመራ ኦምነሐጀር መንገድ መከፈት በሁለቱን አገራት ህዝቦች ለመፍጠር የታቀደውን ጠንካራ የግንኙነት ሰንሰለት በማጥበቅ ረገድ ሚናው የጎላ አንደሆነም ዶክተር ደብረፂዮን ተናግረዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ መንገዱ እንዲከፈት ጥረት ሲያደረጉ መቆየቱን ጠቁመው፤ ዛሬ ላይ ይህ እውን በመሆኑ መደሰታቸውን ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም