ፈቃድ ወስደው ወደ ስርጭት ያልገቡ 17 የማህበረሰብ ሬድዮ ጣቢያዎች የብሮድካስት ባለስልጣን አስጠነቀቀ

79

አክሱም ታህሳስ 28/2011 ፈቃድ ወስደው ወደ ስርጭት ያልገቡ 17 የማህበረሰብ ሬድዮ ጣቢያዎች በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ወደ ሥራ ካልገቡ ፍቃዳቸው እንደሚሰረዝ የብሮድካስት ባለስልጣን አስታወቀ፡፡

የማይጨው ከተማና የደብረብርሀን ዩኒቨርሲቲ የማህበረሰብ ሬድዮ ፍቃድ መሰረዙንም ባለስልጣኑ አስታውቋል፡፡

አክሱም ዩኒቨርሲቲ የማህበረሰብ ሬድዮ ጣቢያ ለማቋቋም የጠቅላላ ጉባኤ እና የቦርድ ምርጫ መድረክ ትላንት አካሂዷል፡፡

በመድረኩ ላይ የተገኙት በባለስልጣኑ የመገናኛ ብዙሃን ምዝገባና ፈቃድ ዳይሬክተር አቶ ሙሉጌታ ሲሳይ እንዳሉት በሀገሪቱ ለ50 የማህበረሰብ ሬድዮ ጣቢያዎች ፈቃድ መሰጠቱን ተናግረዋል፡፡

ፍቃድ ከወሰዱት ውስጥ 31 የማህበረሰብ ሬድዮ ጣቢያዎች ወደ ስርጭት መግባታቸውን ጠቁመዋል፡፡

የማይጨው እና የደብረታቦር ዩኒቨርሲቲ ማህበረሰብ ሬድዮ ፈቃድ ወስደው ከአምስት ዓመት በላይ ስርጭት ባለመጀመራቸው ፈቃደቸው መሰረዙን ገልጸዋል፡፡

ፈቃድ ወስደው እስካሁን ወደስርጭት ያልገቡ 17 የማህበረሰብ ሬዲዮ ጣቢያዎች በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ወደ ስርጭት መግባት እንዳለባቸውም አቶ ሙሉጌታ አመልክተዋል፡፡

የኢሮብ፣ ኩናማ፣ ከሚሴ፣ እንጅባራ፣ ሸካ፣ ስልጤና ሌሎችን ጨምሮ 17 የማህበረሰብ ሬድዮ ጣቢያዎች በዚህ ዓመት ስርጭት እንዲጀምሩ በመንግስት በኩል ክትትልና ድጋፍ እንደሚደረግም ዳይሬክተሩ ተናግረዋል።

ባለስልጣኑ በስልጠና፣ በአሰራርና በሙያ ድጋፍ ለማድረግ ዝግጁ መሆኑን የገለጹት አቶ ሙሉጌታ፣ ጣቢያዎቹ በተባለው ጊዜ ውስጥ ወደስርጭት ካልገቡ የተሰጣቸው ፍቃድ እንደሚሰርዝም አስገንዝበዋል፡፡

የአክሱም ዩኒቨርሲቲ የማህበረሰብ ሬድዮ ጣቢያ ለማቋቋም ከባለስልጣኑ ፈቃድ ለማገኘት የፈቃድ ጠያቂውን ማህበረሰብ ፊርማ ማሰባሰብ እንዳለበትም አመልክተዋል፡፡

" ጣቢያው ህጋዊ ተቋም መሆኑን የሚያረጋግጥና የሚተዳደርበት ህግና መመሪያ፣ የሰው ኃይል አደረጃጀት እንዲሁም፣ የማሰራጫ መሳሪያዎችን አስመልክቶ ዩኒቨርሲቲው በአግባቡ የተደራጀ መረጃ ማዘጋጀት አለበት" ብለዋል፡፡

የጣቢያው የቦርድ ሰብሳቢ ሆነው የተመረጡት የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ዶክተር ጸሐየ አስመላሽ በሰጡት አስተያየት ጣቢያው ሥራውን ሲጀምር ለአካባቢው እና ለዩኒቨርሲቲው ማህበረሰብ ቀዳሚ የመረጃ ምንጭ ሆኖ እንደሚያገለግል ገልጸዋል።

"በዋናነት የህብረተሰቡን ፍላጎትና ችግሮች መሰረት ያደረጉ ሥራዎች ይሰራል" ብለዋል።

የማህበረሰብ ሬድዮ ጣቢያው የካባቢውን ባህል፣ ቋንቋ እና እምነት ከማሳደግ ባለፈ በልማት፣ ዴሞክራሲ ግንባታና መልካም አስተዳደርን በማስፈን በኩል የድርሻውን እንደሚወጣም አመልክተዋል፡፡

በተለይ ዩኒቨርሲቲው የሚያከናውናቸው የምርምር እና የማህበረሰባዊ ተኮር ሥራዎችን ለማስፋት ጣቢያው ጠቀሜታ እንዳለው ነው የገለጹት።

የማህበረሰብ ሬድዮ ጣቢያው ከተለያዩ አካባቢዎች ልምድ በመቀመር በአጭር ጊዜ ውስጥ ወደሥራ ለማስገባት እንደሚሰራም ዶክተር ጸሐዬ አመልክተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም