አባት ልጃቸውን ይዘው ሲጓዙ አባትነታቸውን በተጠራጠሩ ሰዎች ድብደባ ደረሰባቸው

48
አዳማ ታህሳስ 5/2011 ከህገ-ወጥ የህጻናት ዝውውር ጋር በተያያዘ በተከሰተ የተሳሳተ መረጃ ምክንያት በአዳማ ከተማ የገዛ ልጃቸውን ይዘው ሲጓዙ በነበሩ አባት ላይ ጥቃት ደረሰ። ህብረተሰቡ በሃሰተኛ ወሬዎች ምክንያት ጉዳት እንዳይደርስ ጥንቃቄ ማድረግ እንዳለበት የከተማው ፖሊስ አሳስቧል። አቶ ግዛቸው ወርቁ የተባሉ አባት ታህሳስ 3 ቀን 2011 ዓ.ም ከቀኑ 9 ሰዓት ተኩል ላይ በአዳማ ከተማ ቀበሌ 13  አገር ሰላም ነው ብለው ልጃቸውን ከትምህርት ቤት ለማምጣት ይሔዳሉ ። ሌላ ጊዜ ልጃቸውን ከትምህርት ቤት የሚያመላልሱት ወላጅ እናቷ የነበሩ ቢሆንም ሌላ ስራ ስላጋጠማቸው ነበር አባት ወደ ትምህርት ቤቱ የሔዱት ። ልጃቸውን ይዘው ወደ ቤታቸው ሲያመሩ በአካባቢው ሰዎች ልጅ ሰርቆ እየሔደ ነው በሚል ምክንያት ከባድ ድብደባ እንደተፈፀመባቸውና ለከፋ ጉዳት እንደተጋለጡ ተናግረዋል ። ”ልጄ ናት ብዬ መታወቂያ ባሳይም ፣ ህፃኗ ደግሞ  አባቴን አትንኩት ብላ ብትጮህም ያለምህረት ደብድበውኛል ” ሲሉ በምሬት ገልፀዋል። "ባለቤቴ መጥታ የልጄን አባት ለምን ትድበድቡታላችሁ እያለች ብትማፀንም የታክሲ ሾፌሮችና ፖሊሶች ሳይቀሩ የድብደባው ተሳታፊ መሆናቸው ከልብ አዝኛለሁ" ብለዋል ። የተጎጂው ባለቤት ወይዘሮ ባዩሽ ጥበቡ በበኩላቸው በከተማዋ እየተናፈሰ ያለው አሉባልታ ሰላማዊ ዜጎቸን ለጉዳት እየዳረገ በመሆኑ ህዝቡን አለአግባብ የሚያሸብሩ ወሬኞች እየታደኑ በህግ ሊጠየቁ ይገባል የሚል መልእክት አስተላልፈዋል ። የአዳማ ከተማ ፖሊሲ አዛዥ ኮማንደር ደረጀ ሙለታ ለኢዜአ እንደገለፁት ህፃናት እየተሰረቁ ኩላሊታቸው እየተሸጠ ነው የሚል አሉባልታ በመዛመቱ የገዛ ልጃቸውን ይዘው ሲሄዱ በነበሩ ወላጅ አባት ላይ ከባድ ድብደባ ተፈጽሟል። በትምህርት ቤትና በእምነት ተቋማት ሳይቀር ህፃናት ልጆች እየተሰረቁ አደጋም እየደረሰባቸው ነው በሚል የሚናፈሰውን ወሬ ሃሰተኛነት ፖሊስ በማረጋገጡ ህብረተሰቡ እንዲረጋጋ ጥሪያቸውን አስተላዋል። ይሔን ተከትሎ በርካታ ቤተሰቦች ልጆቻቸውን ለትምህርትና ለጨዋታ ከቤት ወጥተው ትንሽ ከዘገዩ ጭምር በድንጋጤ ለፖሊስ የሚቀርቡ ጥቆማዎች ቁጥር በመጨመሩ በስራ ላይ ጫና እየፈጠሩ መምጣታቸውን ኮማንደር ደረጀ ይገልፃሉ ። አሉባልታው በከፋ መልኩ በደምበላ ክፍለ ከተማ ኢሬቻ ቀበሌ በሚገኘው ጫካና በሌሎች አካባቢዎች የህፃናት አስከሬን ተገኝቷል የሚል በመሆኑ ፖሊስ ለማጣራት በቦታው ድረስ ዘልቆ በመግባት አሰሳ ቢያካሔድም ምንም የተገኘ ነገር የለም ብለዋል ።  
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም