አርብቶ አደሩንና አባሎቼን በአግባቡ ከጎኔ ባለማሰለፌ የሚፈለገው ለውጥ አልመጣም...አብዴፓ

106
ሰመራ ህዳር 24/2011 የአፋር ብሔራዊ ዴሞክራሲዊ ፓርቲ /አብዴፓ አባላቱንና አርብቶ አደሩን በሚፈለገው ደረጃ ከጎኑ ባለማሰለፉ የህዝቡ ኑሮ የሚጠበቀውን ያክል እንዳልተለወጠ ገለጸ። ፓርቲው 7ኛው መደበኛ ጉባኤውን ዛሬ በሰመራ ከተማ ማካሔድ ጀምሯል። በጉባኤው መክፈቻ ላይ የፓርቲው ሊቀመንበር አቶ ስዩም አወል እንደተናገሩት አብዴፓ ባለፉት አመታት ህዝቡን ባሳተፈ መልኩ ክልሉን ለመምራት ያደረገው እንቅስቃሴ የሚፈለገውን ውጤት አላስገኘም። የክልሉን አርብቶ አደርና አባላቱን በሚፈለገው ደረጃ ከጎኑ ማሰለፍ ባለመቻሉም የህዝቡን ኖሮ የሚጠበቀውን ያክል መለወጥ እንዳልቻለ ተናግረዋል። አብዴፓ በስትራቴጂክ አመራርነት፣ በውስጠ ድርጅት ዴሞክራሲ፣ በህግ የበላይትና በተደራጀ ሌብነት አንዲሁም በግልና በቡድን የስልጣን ሽኩቻ መኖሩን በማዕከላዊ ኮሜቴ ደረጃና በቅርቡ ባካሄደው ድርጅታዊ ኮንፈረንስ መግባባት ላይ መደረሱን ሊቀመንበሩ አስታውሰዋል፡፡ የፓርቲውን የውስጥ ችግሮች ከመፍታት ባለፈ የህዝቡን ኑሮ ለመለወጥና ከወጣቱ የሚነሱትን ጥያቄዎች ለመመለስ ጉባኤው አቅጣጫ በማስቀመጥ የሪፎርም ስራዎችን ለማከናወን ፓርቲው ቁርጠኛ መሆኑን አቶ ስዩም ተናግረዋል፡፡ ጉባኤው 2ኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን አቅድን ጨምሮ ያለፉትን ሶስት አመታት የፓርቲውን የስራ አፈጻጸም በመገምገም ቀጣይ አቅጣጫዎችን እንደሚያስቀምጥ አቶ ስዩም ጠቁመዋል። የፓርቲውን ነባር አመራሮች በክብር በመሸኘት የተሻለ የትምህርት ዝግጅትና ልምድ ያላቸውን ወጣት አመራሮች እንደሚተካም ሊቀመንበሩ ተናግረዋል፡፡ በጉባኤው ላይ በመገኘት ንግግር ያደረጉት የኢትዮጵያ ህዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲዊ ግንባር /ኢህአዴግ ተወካይ አቶ ፍቃዱ ተሰማ  የተጀመረው ሀገራዊ ለውጥ በህዝቦች ግንባር ቀደም ቀስቃሸነት የመጣ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ "ለሀገራዊ ለውጡ ባለቤቱም ሆነ ጠባቂው የኢትዮጵያ ህዝብ ነው" ያሉት ተወካዩ የአፋር ክልል ህዝብ እንደማንኛውም የሀገሪቱ  ህዝቦች ለውጡን የሚደግፍ ብቻ ሳይሆን ለለውጡ መምጣትና ቀጣይነት የድርሻውን እየተወጣ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ ለውጡን የሚፈታተኑ ግዜያዊ ችግሮችን ለመፍታት በሚደረገው ጥረት የአፋር ህዝብ በትኩረት ሊሰራ እንደሚገባ  አመልክተዋል፡፡ በጉባኤው የኢህአዴግ አህት ድርጅቶችን ጨምሮ፣ ሌሎች የአጋር ድርጅቶችና በክልሉ በሰላማዊ መንገድ የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ፓርቲዎች የድጋፍ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም