በአፋር ክልል በህገ ወጥ መንገድ ሲጓጓዝ የነበረ 10 ሚሊዮን ብር በቁጥጥር ስር ዋለ

118
አዲስ አበባ ህዳር 24/2011 በአፋር ክልል በህገ ወጥ መንገድ ሲጓጓዝ የነበረ 10 ሚሊዮን  ብር በክልሉ ፖሊስ በቁጥጥር ስር መዋሉን የገቢዎች ሚኒስቴር አስታወቀ። የሚኒስቴሩ የኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ አዲሱ ይርጋ ለኢዜአ እንደገለጹት 3 ኩንታል ብር በህገ ወጥ መንገድ ሲጓጓዝ በአፋር ክልል ፖሊስ በቁጥጥር ስር ውሏል። ገንዘቡ ከቡና ኢንተርናሽናል ሎጊያ ቅርንጫፍ ወጪ ተደርጎ በአንድ የባንክ ስራተኛ አማካይነት በቪትስ እና በፒክ አፕ ተሽከርካሪ ያለ አጃቢ በህግ ወጥ መንገድ ሲጓጓዝ በቁጥጥር ሥር መዋሉን ገልጸዋል። ገንዘቡን በህገ ወጥ መንገድ ሊያዘዋውሩ የነበሩት ግለሰቦች ከፖሊስ ለቀረበላቸው ጥያቄ ገንዘቡ ወደ ደሴ ቅርንጫፍ የሚዛወር ነው ቢሉም ገንዘቡ ያለ አጃቢ በህገ ወጥ መንገድ እየተንቀሳቀሰ ያለ በመሆኑ የክልሉ ፖሊስ በቁጥጥር ስር ማዋሉን አስረድተዋል። ድርጊቱን ፈጽመዋል የተባሉት ግለሰቦችም በቁጥጥር ስር ውለው ፖሊስ ጉዳዩን እያጣራ እንደሆነም አቶ አዲሱ ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም