በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ለጸጥታ መደፍረስ ምክንያት የሆኑ አመራሮች ላይ እርምጃ ይወሰዳል---ቤጉህዴፓ

90
አሶሳ ህዳር 24/2011 የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ህዝቦች ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ/ቤጉህዴፓ ማዕከላዊ ኮሚቴ በክልሉ ለተከሰተው የጸጥታ መደፍረስ ምክንያት የሆኑ አመራሮች ተለይተው እርምጃ እንዲወሰድባቸው መወሰኑን አስታወቀ። ባለፈው ቅዳሜ የተጀመረው የፓርቲው ማዕከላዊ ኮሚቴ መደበኛ ስብሰባ እንደቀጠለ ነው፡፡ የፓርቲው ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ዚያድ አብዱላሂ ለኢዜአ እንዳስታወቁት ማዕከላዊ ኮሚቴው በሁለት ቀናት ውይይቱ በክልሉ የጸጥታ ሁኔታ ላይ ተወያይቶ ውሳኔ አሳልፏል ። በክልሉ ለተከሰተው የፀጥታ ችግር ምክንያት የሆኑ አመራሮች ተለይተው ተጠያቂ እንዲሆኑ ውሳኔ ማሳለፉን ተናግረዋል ። "በክልሉ የተከሰተው የጸጥታ ችግር የህብረተሰቡን ደህንነት አደጋ ላይ የጣለ እንደሆነ ማእከላዊ ኮሚቴው በጥልቀት ገምግሟል" ያሉት ሃላፊው ለችግሩ ምክንያት የሆኑ ውስጣዊና ውጫዊ ችግሮች መለየታቸውን ጠቁመዋል፡፡ ማዕከላዊ ኮሚቴው ግምገማውን በውስጣዊ ችግሮች ላይ በማተኮር  አመራሩን የሚመለከቱ ጉዳዮችን መመልከቱን ገልፀዋል ። "የህግ የበላይነትን ለማስፈን በተደረገ ጥረት በኩል የነበሩ ጉድለቶች በውይይቱ መለየታቸውን ተናግረዋል ። በክልሉ አሶሳ፣ ቶንጎ፣ ኩርሙክ፣ አልመሃል ከተሞችና ካማሽ ዞን ሆን ብለው ግጭቶችን ያስነሱና በድርጊቱ የተሳተፉ በክልሉ የተለያዩ መዋቅሮች ውስጥ ያሉ አካላትን ለህግ በማቅረብ በኩል የነበሩ ጉድለቶች በግምገማው መለየታውን ለአብነት ጠቅሰዋል ። በክልሉ ሥራ አጥነትን ለመቀነስ ጥረት ቢኖርም የወጣቱን ጥያቄ በአግባቡ እንዳልተመለሰ በውይይቱ የተለየ ሌላው ክፍተት መሆኑን ኃላፊው ተናግረዋል ። በኢንቨስትመንት ስም የክልሉን የተፈጥሮ ሃብት ሲቀራመቱ የነበሩ ጥገኛ ሃይሎች ተግባራቸው እንዲቋረጥ በመደረጉ ወጣቶችን በብሄር በመከፋፈል እርስ በርስ በማጋጨት ለህይወትና ለንብረት ጥፋት ምክንያት መሆናቸው መለየቱንም ጠቅሰዋል ። "እነዚሁ ኃይሎች ክልሉን ከማተራመስ ባሻገር ሀገራዊ ለውጡን የማደናቀፍ ግብ እንደነበራቸው ማዕከላዊ ኮሚቴው በጥልቀት ተገንዝቧል" ብለዋል ። "ክልሉ ከኦሮሚያ በሚዋሰንባቸው አካባቢዎች በሚታዩ ግጭቶች ሳቢያ በተፈጠረው የመንገድ መዘጋት ከክልሉ አቅም በላይ በመሆኑ በክልሉ ሰባት ወረዳዎች እርዳታ ለማድረስም ሆነ  የመብት ጥሰቶችን ለማስቆም እንዳልተቻለ ኮሚቴው ተመልከቷል " ሲሉም ተናግረዋል ። እንደ ኃላፊው ገለጻ የማዕከላዊ ኮሚቴው ግምገማ በጥቅሉ ባለፉት 27 ዓመታት የክልሉ ነባራዊ ሁኔታ ህዝቡ በሚፈለገው መልክ አለመቀየሩን አረጋግጧል። እያንዳንዱ አመራር ኃላፊነቱን የተወጣበት አግባብና ከጸጥታ ችግሮች ጀርባ እጁ መኖር አለመኖሩን በመለየት ዘላቂ መፍትሄ ለማምጣት ማዕከላዊ ኮሚቴው ድምዳሜ ላይ መድረሱንም ጠቁመዋል፡፡ ችግሮቹን ለመፍታት የአጭርና የረዥም ጊዜ አቅጣጫ እንዳስቀመጠ የገለጹት ኃላፊው በቅርቡ የአመራር ለውጥ እንደሚያስፈልግ ማዕከላዊ ኮሚቴው መወሰኑን አስታውቀዋል ። “በክልሉ ቀውስ ሲፈጠር ተስፋ የሚቆርጥ እንጂ ፈጥኖ መፍትሄ የሚሰጥ አመራር አለመፈጠሩን ማዕከላዊ ኮሚቴው አረጋግጧል” ያሉት ኃላፊው ማዕከላዊ ኮሜቴው ሁኔታውን ለመቀየር የሚያሰችሉ አቅጣጫዎች ላይ ተወያይቶ ውሳኔ እንደሚያሳልፍ አመላክተዋል ። የማዕከላዊ ኮሚቴው ስብሰባ ለቀጣይ ሁለት ቀናት እንደሚቀጥል ታውቋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም