በሃዋሳ ከተማ ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ አስተዳደሩን ያሳወቀ አካል የለም - የከተማ አስተዳደሩ ፖሊስ መምሪያ

104
ሃዋሳ ህዳር 17/2011 ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ  የከተማ አስተዳደሩን ያሳወቀ አካል አለመኖሩን የሃዋሳ ከተማ አስተዳደር ፖሊስ መምሪያ አስታወቀ፡፡ 'በሃዋሳ ከተማ ሰላማዊ ሰልፍ ይደረጋል' ተብሎ  በተሰራጨው ሃሰተኛ ወሬ ስጋት የገባቸው አንዳንድ ማህበራዊ አገልግሎት ሰጪና የንግድ ተቋማት ተዘግተው ማርፈዳቸውን ፖሊስ ገልጿል፡፡ የከተማ አስተዳደሩ ፖሊስ አዛዥ ኮማንደር መስፍን ዶብሶ እንዳሉት ''ሰላማዊ ሰልፍ አደርጋለሁ'' በሚል  የከተማውን አስተዳደር ያሳወቀ አካል የለም፡፡ ይሁን እንጂ በሃዋሳ ከተማ ሰላማዊ ሰልፍ ይደረጋል ተብሎ በተሰራጨው ሃሰተኛ ወሬ ስጋት የገባቸው አንዳንድ ማህበራዊ አገልግሎት ሰጪና የንግድ  ተቋማት ዛሬ ተዘግተው አርፍደዋል፡፡ የተወሰኑ የከተማው ነዋሪዎችም ልጆቻቸውን ወደ ትምህርት ቤት አለመላካቸውን በመግለጫቸው ተናግረዋል፡፡ ''የተናፈሰውን አሉባልታ በመስማት የከተማው ነዋሪዎች ልጆቻቸውን ትምህርት ቤት  ያለመላክና ሱቆቻቸውን የመዝጋት  እርምጃ መውሰዳቸው ተገቢ አይደለም' ያሉት ኮማንደር መስፍን 'የሃዋሳ ከተማ ፍፁም ሰላማዊ ነው'' ሲሉ ገልፀዋል፡፡ በመሆኑም የተዘጉ ቤቶች እንዲከፈቱ፣ ማህበራዊ አገልግሎት ሰጪ ተቋማትና የከተማው ነዋሪዎች መደበኛ ኑሮውን ያለስጋት እንዲቀጥል አሳስበዋል፡፡ በከተማው አንዳንድ አካባቢዎች ንግድ ቤቶችን በማስፈራራትና በመዝጋት ገንዘብ የመውሰድና ባነሮችን አውርዶ የማውደም ወንጀሎች እየተፈፀሙ ነው የሚል ከጋዜጠኞች ለቀረበላቸው ጥያቄም ፖሊስ አዛዡ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ አዛዡ በሰጡት ምላሽም ነዋሪው በሰላም ወጥቶ እንዳይገባና በስጋት እንዲኖር በሚያደርጉና በተመሳሳይ ወንጀል የተሳተፉ ግለሰቦች በቁጥጥር ስር እየዋሉ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ለአብነትም ከማውንቴን ስናክ ጎን በሚገኘው አንድነት ስጋ ቤት ዛሬ ጠዋት የዝርፊያ ወንጀል መፈጸሙንና በዚህ ወንጀል ውስጥ የተሳተፈ አንድ ግለሰብ በቁጥጥር ስር መዋሉን ገልጸዋል፡፡ የተቀሩት ሁለት ተጠርጣሪዎች እየተፈለጉ መሆናቸውን ፖሊስ አዛዡ ተናግረዋል፡፡ በከተማው በሞተር ሳይክል እየተንቀሳቀሱ ሁከት የሚፈጥሩና ከተማውን የሚያውኩ ግለሰቦች ከድርጊታቸው እንዲቆጠቡ አሳስበዋል፡፡ ከወንጀሉ ድርጊት ጀርባ ያለውን ሃይል ፖሊስ ክትትል እያደረገ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡ የከተማው ህዝብ በሰላም ወጥቶ በሰላም እንዲገባ ነዋሪዎች ጥቆማ በመስጠት ከፖሊስ ጎን እንድቆሙ ፖሊስ አዛዡ ጠይቀዋል፡፡                  
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም