ከአሶሳ ዩኒቨርሲቲ ግጭት ጋር በተያያዘ ሶስት የፖሊስ አባላት በቁጥጥር ሥር ዋሉ

106
አሶሳ ህዳር 16/2011 በአሶሳ ዩኒቨርሲቲ ግጭት ተጠርጥሮ በቁጥጥር ሥር የዋለው ግለሰብ “ታምሚያለሁ” በሚል ወደ መኖሪያ ቤቱ እንዲሄድ በመፍቀድ በግለሰቡና በጸጥታ ሃይሎች መካከል ውጥረት እንዲፈጠር አድርገዋል በሚል የተጠረጠሩ ሶስት የፖሊስ አባላት በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን የአሶሳ ከተማ ፖሊስ መምሪያ አስታወቀ፡፡ የአሶሳ ከተማ ፖሊስ አዛዥ ኮማደር አኑር ሙስጣፋ ለኢዜአ እንዳስታወቁት በከተማው የወረዳ ሁለት መደበኛ ፖሊስ አባላት የሆኑ ሶስት ግለሰቦች ማምሻውን ትጥቃቸውን ፈትተው በቁጥጥር ሥር ውለዋል፡፡ የፖሊስ አባላቱ በቁጥጥር ሥር የዋሉት በአሶሳ ዩኒቨርሲቲ ግጭት ተጠርጥሮ በቁጥጥር ሥር የዋለው ግለሰብ ላቀረበው የ”ታምሚያለሁ” ጥያቄ ጉዳዩ ከሚመለከተው የወረዳው አካል ትዕዛዝ ሳያገኙ በራሳቸው ፈቃድ ግለሰቡን ወደ መኖሪያ ቤቱ በመውሰዳቸው ነው፡፡ የጸጥታ ሃይሎቹ ተጠርጣሪውን ወደ ህክምና ተቋም መውሰድ ሲገባቸው ወደ መኖሪያ ቤቱ መውሰድ እንዳልነበረባቸው ኮማንደር አኑር አስረድተዋል፡፡ ግለሰቡም ወደ መኖሪያ ቤቱ በተወሰደበት ወቅት ክላሽንኮብ በማውጣት በጸጥታ ሃይሎች ላይ ጥቃት ለማድረስ ሙከራ ማድረጉን አስረድተዋል፡፡ ይህንኑ ተከትሎ በከተማው በተወሰኑ ቦታዎች አለመረጋጋት ታይቶ እንደነበረ ጠቅሰው በአሁኑ ወቅት ግን የከተማው ሁኔታ በጸጥታ ሃይሎች እና በህብረተሰቡ ትብብር ወደ ነበረበት እንደተመለሰ አስታውቀዋል፡፡  
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም