የነቀምቴ የኢሬቻ በዓል አከባበር የዴሞክራሲ ስርዓት እያበበ ስለመምጣቱ የታየበት ነው---አባ ገዳዎች

121
ነቀምቴ ጥቅምት25/2011 በነቀምቴ የዘንድሮ ኢሬቻ በዓል አከባበር በአገሪቱ የዲሞኪራሲ ሥርአት ግንባታው እያበበ ስለመምጣቱ የታየበት ነው ሲሉ አባ ገዳዎች ገለፁ። በነቀምቴ ሀዲያ የኢሬቻ በዓል ዛሬ በድምቀት ተከብሯል ። የሌቃ አባ ገዳ አስፋው ከበደ በወቅቱ እንደገለጹት ባለፉት ዓመታት በአካባቢው የኢሬቻ በዓል በድብቅና በውስን ግለሰቦች ብቻ ሲከበር ቆይቷል። "በዛሬው እለት ከፍተኛ ቁጥር ያለው ህዝብ በይፋና በድምቀት በዓሉን አክብሯል" ያሉት አባ ገዳ አስፋው የዘንድሮ የበዓሉ አከባበር በአገሪቱ የዴሞክራሲ ስርአት ግንባታ እያበበ ስለመምጣቱ ያሳየ መሆኑን ተናግረዋል ። አባገዳ ምስጋኑ ለሚ በበኩላቸው "የዘንድሮ የኢሬቻ በዓል በአገሪቱ የፍቅርና የአንድነት ጉዞ በተቀጣጠለበትና የዴሞኪራሲ ስርአት ግንባታው ማበብ በጀመረበት ወቅት መከበሩ ልዩ ያደርገዋል " ብለዋል ። አባገዳዎች፣ ቄሮዎችና መላው ታዳሚ  በዓሉን በፍቅርና በአንድነት እንዳከበሩት የገለጹት አባገዳ ምስጋኑ ህዝቡ በበዓሉ ላይ ያሳየውን የመከባበርና የአንድነት ባህል በዕለት ተዕለት እንቅስቃሴዎም አጠናክሮ እንዲያስቀጥል ጠይቀዋል። የዘንድሮ የኢሬቻ በዓልን ህዝቡ በብዛት ተግኝቶ በነጻነት ማክበሩ ዴሞክራሲያዊ መብቱን እየተረጋገጠለት መሆኑን ያሳያል ያሉት አባገዳ ምስጉን ህዝቡ የህግ የበላይነትን በማክበር ለባህላዊ እሴቱ መጎልበት የድርሻውን እንዲወጣም መልዕክት አስተላልፈዋል ። ወጣት ሙሉዓለም ታደሰ በበኩሉ "የዘንድሮ ኢሬቻ በዓል ያለ ማንም ወገን ጣልቃ ገብነት በህብረተሰቡ ዘንድ በሰላም ተከብሯል " ብሏል ። "በዓሉ የኦሮሞ ብሔር ተወላጆች ከሌሎች ኢትዮጵያውያን ወገኖቻቸው ጋር ያላቸውን ግንኙነት ያጠናከሩበት ነበር " ሲልም ወጣቱ  ገልጿል ። " ዘንድሮ የኢሬቻ በዓል ከወትሮ በተለየ መልኩ  ከአዳማ፣ ከቦረናና ከሌሎች አካባቢዎች የተወከሉ ወጣቶችና የአገር ሽማግሌዎች የታደሙበት ነበር"  ያለው ደግሞ ወጣት ድንቃ ገእሳ ነው ። በበዓሉ ክብረ በዓል ላይ ከተለያዩ አከባቢዎች የተውጣጡ የህብረተሰብ ክፍሎች መታደማቸው ከዚህ ቀደም የነበረው የስጋትና የፀጥታ ችግር እየተፈታ መምጣቱን የሚያሳይ መሆኑንም ገልጿል። በነቀምቴ "በሃዲያ" በሚባል ሥፍራ ዛሬ በተከበረው የኢሬቻ በዓል ላይ በርካታ ህዝብ መታደመበት ነው ።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም