የአብርሆት ቤተ መጻሕፍት እስከ ሌሊት 6 ሰዓት አገልግሎት መስጠት ሊጀምር ነው - ኢዜአ አማርኛ
የአብርሆት ቤተ መጻሕፍት እስከ ሌሊት 6 ሰዓት አገልግሎት መስጠት ሊጀምር ነው
አዲስ አበባ (ኢዜአ) ሕዳር 13/2015 የአብርሆት ቤተ መጻሕፍት ከነገ ህዳር 14 ቀን 2015 ዓ.ም ጀምሮ እስከ ሌሊት 6 ሰዓት አገልግሎት ለመስጠት ዝግጅት ማጠናቀቁ ተገለጸ።
የአብርሆት ቤተ መጻሕፍት ዳይሬክተር ኢንጂነር ውባየሁ ማሞ እንዳሉት ቤተ መጻሕፍቱ ኢትዮጵያን የሚያኮራ ታሪክ ሰሪ ትውልድ በንባብ የሚገነባበት ማዕከል ነው ።
በንግግርና ውይይት የሚያምን ትውልድ የሚገነባው አንባቢ ትውልድ ሲፈጠር መሆኑን ጠቅሰው፤ የአብርሆት ቤተ መጻሕፍት አንባቢ ትውልድን ለማፍራት ትልቅ ድርሻ አለው ብለዋል።
ቤተ መጻሕፍቱ ከዚህ ቀደም ከጧቱ 2 ሰዓት እስከ 12 ብቻ አገልግሎት ይሰጥ እንደነበር አውስተው ተጠቃሚዎች የአገልግሎት ሰዓት እንዲራዘም ሲጠይቁ እንደነበርም ጠቁመዋል።
ይህን ከግምት ውስጥ በማስገባትም አገልግሎት የሚሰጥበት ሰዓት ማሻሻያ መደረጉን ጠቅሰዋል።
በመሆኑም ከነገ ጀምሮ ከጧቱ 2 ሰዓት እስከ ሌሊቱ 6 ሰዓት ድረስ ቤተ መጻሕፍቱ ለህዝብ ክፍት እንደሚሆን ነው የተናገሩት።
በተያያዘ ዜና በኬንያ የኢትዮጵያ ኮሚኒቲ አባላት የተሰባሰበ መጻህፍት በኬንያ ዲያስፖራና የቆንስላ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አምባሳደር ዶክተር ደስታ ወልደዮሐንስ በኩል ለቤተ- መጽሐፍቱ ተበርክቷል።
በዛሬው እለት የተሰጡት 164 መጻህፍት መሆናቸውንና በተለያዩ ርዕሰ-ጉዳዮች የተጻፉ መሆናቸውንም አምባሳደሯ ተናግረዋል።
ከዚህ በተጨማሪ 500 የሚሆኑ መጻህፍት በኬንያ የኢትዮጵያ አምባሳደር ጄነራል ባጫ ደበሌ የተሰበሰቡ እንዳሉ በመጥቀስ በቅርቡ ለቤተ-መጽሐፍቱ እንደሚደርሱ ነው የገለጹት።
የአብርሆት ቤተ-መጽሐፍት ዳይሬክተር ኢንጂነር ውባየሁ ማሞ፤ ለቤተ-መጽሐፍቱ ከሀገር ውስጥ በተጨማሪ በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን መሰል መጻህፍትን በማሰባሰብ ስጦታ እንዲያበረክቱ ጠይቀዋል።
የአብርሆት ቤተ-መጽሐፍት ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀና የሚያምር የኪነ-ህንጻ ጥበብ ሥራ አርፎበት ከ1 ነጥብ 1 ቢሊየን ብር በላይ ወጭ የተገነባ መሆኑ ይታወቃል።