በቀን ከ30 ሺህ ሊትር በላይ የማምረት አቅም ያለው “ዩኒሰን” የምግብ ዘይት ፋብሪካ ተመርቆ ስራ ጀመረ

438

ባህር ዳር (ኢዜአ) ህዳር 4/2015 በባህር ዳር ከተማ በቀን ከ30 ሺህ ሊትር በላይ የማምረት አቅም ያለው “ዩኒሰን” የምግብ ዘይት ፋብሪካ የክልሉ ርዕሰ መስተዳደር ዶክተር ይልቃል ከፋለ በተገኙበት ተመርቆ ማምረት ጀመረ።

ፋብሪካው 1 ነጥብ 5 ቢሊየን ብር ወጭ የተደረገበትና የሀገር ውስጥ ጥሬ እቃዎችን በመጠቀም የምግብ ዘይት እንዲያመርት ታሳቢ ተደርጎ የተገነባ ነው።

ፋብሪካው አኩሪ አተር፣ ሱፍ፣ ሰሊጥ፣ ኑግ፣ ለውዝና ሌሎች የሀገርው ውስጥ የቅባት እህሎችን በመጠቀም ማምረት የሚችል መሆኑ ተገልጿል።

ፋብሪካው በሰፊው ምርት በማምረት በአቅርቦትም ሆነ በዋጋ የማህበረሰቡን የዘይት አቅርቦት ችግር ለመቅረፍ አላማ ይዞ ስራ የጀመረ መሆኑንም ተመላክቷል።

በምረቃ ስነ-ስርዓቱ የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳደርን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግስት የስራ ሃላፊዎችና ባለሃብቶች ተገኝተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም