የቴክኒክና ሙያ ተቋማት የጥራት ማረጋገጫ ሰርተፍኬት እንዲያገኙ እየተሰራ ነው- የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር

98

መስከረም 22 /2015 (ኢዜአ) የቴክኒክና ሙያ ተቋማት የጥራት ማረጋገጫ ሰርተፍኬት እንዲያገኙ እየተሰራ መሆኑን የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር አስታወቀ።

የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል ከተለያዩ ክልሎች ከተውጣጡ የፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ ዲኖች ጋር ውይይት ውይይት አድርገዋል ።

የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር የክህሎት ክፍተትን መነሻ ያደረጉ ሥልጠናዎችን ለመስጠት ከተለያዩ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች ጋር የጋራ ሥምምነቶችን መፈራረሙን ሚኒስትሯ ገልጸዋል።

በዚህም የቴክኒክና ሙያ ተቋማቱ ይህንን እድል በተገቢው መንገድ ለመጠቀም አቅማቸውን ማጎልበት እንደሚጠበቅባቸው አሳስበዋል፡፡

የቴክኒክና ሙያ ሥልጠና ራሱን ችሎ እንዲቆምና ተቋማቱ የጥራት ማረጋገጫ ሰርተፍኬት እንዲያገኙ እየተሰራ እንደሚገኝ ነው ያስታወቁት፡፡

በመድረኩ ላይ በቴክኖሎጂ አጠቃቀም፣ በስልጠና ጥራትና ተግባራዊነት እንዲሁም ከኢንዱስትሪዎች ጋር በቂ ትሥሥርን ከመፍጠር አንፃር ሊሻሻሉ በሚገባቸው ጉዳዮች ላይ ውይይት መደረጉን ከሚኒስቴር መስሪያቤቱ የተገኝው መረጃ ይጠቁማል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም