ለቢሾፍቱው የሆራ አርሰዴ ኢሬቻ በዓል አከባበር እንግዶች ወደ ከተማዋ እየገቡ ነው

124

መስከረም 21 2015 (ኢዜአ) ነገ በቢሾፍቱ በድምቀት ለሚከበረው የሆራ አርሰዴ ኢሬቻ በዓል ለማክበር እንግዶች ወደ ከተማዋ በመግባት ላይ ናቸው ።

በዚህ የኦሮሞ ገዳ ስርዓት አካል በሆነው የኢሬቻ በዓል ለመታደም ከተለያዩ የኢትዮጵያ ክፍልና የኦሮሚያ ክልል የመጡ እንግዶች ይታደማሉ ተብሎ ይጠበቃል።

የኦሮሞ አባገዳዎች፣ ሀደ ሲንቄዎች፣ወጣቶች እና ሌሎች የሕብረተሰብ ክፍሎች ባማሩ አልባሳት ደምቀውና ተውበው ወደ ከተማው በመግባት ላይ ይገኛሉ።

ሆቴል፣ግሮሰሪ፣የእንግዳ ማረፊያ፣ምግብ ቤቶችና ሌሎች ማህበራዊ አገልግሎት ሰጪ ተቋማት እንግዶችን ተቀብለው እያስተናገዱ ነው።

ነገ ጠዋት በሆራ አርሰዲ ሐይቅ በሚኖረው ስነ ስርዓት የባህሉ በሚፈቅደው መሰረት የክረምቱ ጨለማ አልፎ በብርሃን መተካቱን ለማብሰር ለፈጣሪ ምስጋና ይቀርባል።

የኢሬቻ በዓል ምስጋና፣ፍቅር፣ሰላም፣እርቅ እና ይቅርታ የሚሰበክበት፤ በትውልድ ቅብብሎሽ ውስጥ ዘመናትን ተሻግሮ የኦሮሞ ሕዝብ የሰላምና አንድነት ምልክት ሆኖ ዘልቋል።

የሆራ ፊንፊኔ ኢሬቻ በዓል ዛሬ በአዲስ አበባ ከተማ በድምቀት መከበሩ ይታወቃል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም