የሳርቤት - ጎፋ ማዞርያ - ፑሽኪን ጎተራ ማሳለጫ መንገድ ለተሻለ የትራፊክ ፍሰትና ለከተማዋም ውበት የሚሆን ነው - ኢንጅነር ሞገስ ጥበቡ

187

ነሐሴ 09 ቀን 2014(ኢዜአ) የሳርቤት - ጎፋ ማዞርያ - የፑሽኪን ጎተራ ማሳለጫ ዘመናዊ መንገድ የትራፊክ መጨናነቅን በከፍተኛ ሁኔታ ከመቀነስ ባሻገር ለከተማዋ አዲስ ገጽታ የሚያላብስ መሆኑን የአዲስ አበባ ከተማ መንገዶች ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጅነር ሞገስ ጥበቡ ገለጹ።

የሳርቤት - ጎፋ ማዞርያ - የፑሽኪን ጎተራ ማሳለጫ ዘመናዊ የመንገድ ፕሮጀክት ተመርቋል።

በምረቃ መርሐግብሩ ላይ ንግግር ያደረጉት አዲስ አበባ ከተማ መንገዶች ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጅነር ሞገስ ጥበቡ የመንገዱ መጠናቀቅ ለአዲስ አበባ ከተማ አዲስ ገጽታ አላብሷታል ብለዋል።

የሳርቤት - ጎፋ ማዞርያ - የፑሽኪን ጎተራ ማሳለጫ ዘመናዊ የመንገድ ፕሮጀክት 3 ነጥብ 8 ኪሎሜትር ርዝመት ያለው መንገድ መሆኑንም ገልጸዋል።

የመንገዱ የጎን ስፋትም ከ30 እሰከ 46 ሜትር መሆኑም አንስተው የውስጥ ለውስጥ መተላለፊያ ዋሻ 320 ሜትር ርዝመት እንዳለው ተናግረዋል።

ለዚህ የመንገድ ፕሮጀክት 1 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር ወጪ የተደረገ ሲሆን በሁለት ዓመት ተኩል ጊዜ ውስጥ መጠናቀቁንም ገልጸዋል።

የመንገድ ፕሮጀክቱን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ፣ የገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ፣ የትራንስፖርት እና ሎጀስቲክ ሚኒሰትር ዳግማዊት ሞገስ እና ሌሎች ከፍተኛ የመንግስት የስራ ሃላፊዎች በተገኙበት በዛሬው እለት ተመርቋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም